Wednesday, October 28, 2015

ኢህአዴግ አክራሪ የኒዮሊበራል ሀይሎች የግብርና ኢንቨስትመንቴን እየጎዱብኝ ነው አለ


ጥቅምት ፲፯ (አስራ ሰባት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የሀገር ውስጥና የዉጪ ሀገር ባለሀብቶች በሰፋፊ እርሻዎች ላይ እንዲሰማሩ ባለፉት አምስት አመታት ከፍተኛ ጥረት ቢደረግም የኒዮሊበራል ሀይሎች ባካሄዱት ፕሮፖጋንዳ ምክንያት ውጤት ማግኘት አልቻልኩም ሲል አማሯል።
ከግንባሩ የተገኘ አንድ የግምገማ ሰነድ ፣ የሀገር ውስጥና የውጪ ባለሀብቶች በቆላማ አካባቢዎች በኮሜርሻል እርሻዎች እንዲሳተፉ አስፈላጊው ድጋፍ ቢደረግም ፣ አንዳንዶቹ በእድሉ ተጠቅመው ጥሩ እያመረቱ ቢሆንም፣ ሌሎች ግን ከስረው ከስርአቱ ለመውጣት እየተዘጋጁ ነው ብሎአል።
ሰነዱ “አዳዲስ ባለሀብቶች ወደዘርፉ ለማስገባት የሚደረገውን ጥረት አክራሪ የኒዮሊበራል ሃይሎች “መሬት ተወረረ፣ ህዝብ ተፈናቀለ” እያሉ በሚነዙት የበሬ ወለደ ዘመቻ መደናገር ያለ በመሆኑ እንዳሰብነው አልተሳካም “ይላል። አንዳንድ ባለሀብቶች ይህንኑ ዘመቻ ወደጎን ብለው የመጡ ቢሆንም፣ በአካባቢዎቹ በቂ መሰረተልማት ባለመሙዋላቱ በተገቢው ሁኔታ ማሳተፍ እንዳልተቻለ ይገልጳል። በአሁኑ ሰአት ከእነ ጉድለቱም ቢሆን ግማሽ ሚሊየን ሄክታር መሬት በባለሀብቶች እየለማ ነው ሲል አክሏል።
ኢህአዴግ ስርአቱን የሚቃወሙትን ወይም የሚፈጽመውን የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን የሚያጋልጡትን አለማቀፍ ድርጅቶችም ጭምር የኒዎ ሊበራል ወኪሎች ይላቸዋል።

Source:: Ethsat

No comments:

Post a Comment