Friday, July 3, 2015

ኢሳት ቴሌቪዥን ስርጭቱን በአዲስ ሳተላይት እንደገና ጀመረ


ሰኔ ፳፮ (ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-ከአንድ ወር በላይ ተቋርጦ የነበረው የኢሳት ቴሌቪዥን አገልግሎት በአዲስ ሳተለይት ስራ ጀምሯል። ከኢህአዴግ መንግስት በሚደርስበት ከፍተኛ ጫና የተነሳ ስርጭቱ በተደጋጋሚ ሲቋረጥ የቆየው ኢሳት ቴሌቪዥን ኤ ኤም 44 በሚባል ሳተላይት የቴሌቪዥን ስርጭቱን ከትናንት ሰኔ 25፣ 2007 ዓም ጀምሮ እንደገና ጀምሯል።
በአለማቀፍ የፕሬስ ድርጅቶች ሳይቀር ሃሳብን በማፈን የሚወነጀለው የኢህአዴግ መንግስት የኢሳትን ስርጭቶች በቀጥታ የአፈና ሙከራ፣ በዲፕሎማሲያዊ ዘመቻ እንዲሁም ለተለያዩ ኩባንያዎች ከፍተኛ የመደለያ ገንዘብ በመስጠት ስርጭቱ በኢትዮጵያ እንዳይታይ ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል። አንዳንድ ኩባንያዎች የኢሳትን ስርጭቶች ለማስተላለፍ ፈቃደኛ እንደማይሆኑ በግልጽ መናገር መጀመራቸው፣ ሳተላይት የመፈለጉን ስራ አድካሚ አድርጎት ቆይቷል።
አንዳንድ የሳተላይት ኩባንያዎች ኢሳትን ወደ አየር በማውጣት ከሚያገኙት ጥቅም ይልቅ፣ ኢሳትን በማስቀረታቸው ከመንግስት የሚያገኙት ጥቅም እንደሚበልጥባቸው ይናገራሉ።
በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኝ አንድ የሳተላይት ድርጅት፣ “ከኢሳት ጋር ኮንትራንት የምንፈራረመው፣ የኢትዮጵያ መንግስት ሲፈቅድ ብቻ ነው፣ ምክንያቱም ከኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ የሆነ የቢዝነስ ስምምነት አለን” በማለት ፣ ከኢሳት ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ ሰጥተዋል።
ኢሳት በናይል ሳት የሚያሰራጨው የሬዲዮ ዝግጅት ለተወሰኑ ሳምንታት ተቋርጦ የነበረ ቢሆንም፣ ስራውን እንደገና ጀምሯል።
አዲሱን የኢሳት ቴሌቪዥን ስርጭት በ
AM 44
11 degree West
frequency 11040
symbol rate 22000
fec 3/4
vertical ላይ የምታገኙት መሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን።

No comments:

Post a Comment