Thursday, April 9, 2015

(የየመን ጉዳይ ) ኢትዮጵያዊያን በጦርነቱ እየረገፉ ነው – ጋዜጠኛ ግሩም ተክለሃይማኖት ከየመን እንደዘገበው


yemen1
የመን ጭር ብላለች፡፡ ብዙዎች እየሞቱ ነው፡፤ የሞቱን ጽዋ እየተጎነጩ ያሉት ግን ኢትዮጵያዊያኖችም ጭምር ናቸው፡፡ በጭርታዋ ውስጥ ግን በጦር መሳሪያ የተቀነባበረ ሞቅ ደመቅ ያለ ጩኸት ያናውጣታል፡፡ ከየአቅጣጫው ተኩሱ ርችት መስሎ ያዳምቀዋል፡፡
የየመኗ ዋና ከተማ ሰነዓ ታጥቦ እንደተሰጣ ጨርቅ በመውደቅና ባለመውደቅ መካከል ሆና ትራገባለች፡፡ ያልለመደባትን ዝምታን ተጎናጽፋ ግርግሩ ሁካታው የመኪናው ጩኸት ከስሞ ድብዝዝ ብሎ ደስታዋን የተነጠቀች ልጃገረድ መስላ ፈገግታዋ መወየብ ብቻ ሳይሆን ጠውልጎ ነው ያለችው የየመኗ ሰነዓ፡፡
ነዳጅ የለም፡፡
መብራት ብልጭ ድርግም ሲል ናይት ክለብ ያሉ ያስመስሎታል፡፡ ሱቆች እየተዘጋጉ ነው፡፡ የእቃዎች ዋጋ በእጥፍ ጭምሯል፡፡ ከተማዋ ጭር ብላለች፡፡ ህዝቡ እየሸሸ ወደ ገጠር ገብቷል፡፡ ከተማ ውስጥ ጥቂት የመናዊያን እና ጥቂት ሶማሊያዊያን እና ኢትዮጵያዊያን ናቸው ሰነዓን ያሉባት፡፡
ሰሞኑን በርካታዎች እየረገፉበት ያለው የመን ላይ በሳዑዲ አረቢያ አስተባባሪነት እየተወሰደ ያለው የአየር ጥቃት በርካታ ሲቪሎች እየሞቱ ነው፡፡ ህጻናት በአሰቃቂ ሁኔታ እየተጎዱ ነው፡፡ በአየር ጥቃቱ ኢትዮያዊያንም በተለያየ ቦታ እየተጎዱ ነው፡፡ በተለይ በርካታ ኢትዮጵያዊያ በአደኑ ጦርነት ምክንያት ረግፈዋል፡፡
ያናገርኳቸው አደን ነዋሪ የሆኑ ኢትዮጵያዊያኖች ኮርማክሰር የሚባለው አካባቢ ሜዳው ላይ ካርቶን እየዘረጉ የሚተኙ በርካታ ሱማሊያዊያን እና ኢትዮጵያዊያን እንደተኙ ነው ጦርነቱ በተነሳው፡፡ በዛው ዳግም ያላዩዋቸው ስልክ ቢደውሉላቸው ስልካቸው ዝግ መሆኑን የተባገሩ አሉ፡፡ ክሬተር የተባለ አካባቢ ኢትዮጵያዊኖች የሚኖርበት ህንጻ ተመቶ ሙሉ ለሙሉ ሲጎዳ ውስጡ ከነበሩ 17 ሰዎች መሞታቸው ታውቋል፡፡ ምን ያህሉ ይሆኑ ኢትዮጵያዊ?
….በባህር እየገቡ የነበሩትም በየቦታው የነበሩ ኢትዮጵያዊያን መጎዳታቸው ይገመታል፡፡ በትክክልም በባብል መንድብ አካባቢ የነበሩ ስደተኞች የገቡበት አልታወቀም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቼን ለማስገባች እየመዘገብኩ ነው ቢሊም አመዘጋገባቸው አዝጋሚ መሆኑን ለማጣራት ባደረኩት ሙከራ አረጋግጫለሁ፡፡ ወደ ሀገር የማስገባቱ ሁኔታ ‹‹ቁቅም ከፈስ ተቆጥራ..›› የሚያስተርት ነው፡፡ ከ150.000 በላይ ኢትጵያዊያን ካለበት ቦታ 30 እና 25 ሰው በባህር አሻገርን እየተባለ ፕሮፖጋንዳ ይሰራል፡፡ እንዚህ ሰዎች ግን ከአደን ወደ ኢትዮጵያዊያን ቻይናዎችን ለምነው የተሸገሩ ሲሆኑ የተቀሩት እና አሁንም እየገቡ ያሉት ከሰነዓ ሁዴዳ የተባለው የወደብ ከተማ በመሄድ በግል ወደ ጅቡቲ የሚገቡ ናቸው፡፡
እኔ ባለኝ መረጃ መሰረት ትላንትና ከሰነዓ 14 ሰዎች ወደ ሁዴዳ መሄዳቸው ታውቋል፡፡ በዛሬው ሀሙስ እለት ደግሞ 21 ሰዎች አንድ ሚኒባስ በመኮናተር ወደ ወደብ ከተማዋ ሁዴዳ አምርተዋል፡፡ ማን ያውቃል ነገ እና ዛሬ ማታ በEBC ቲቪ (እንዳሻው ቲቪ እለዋለሁ እኔ እንዳሻው ስለሚቀባጥር) ዜና ላይ እንዚህ በራሳቸው ተንገላተው የገቡትን ዜጎች እናያቸው ይሆናል፡፡
በዚሁ ልክ ሰዉን ‹‹ኑ..›› እያለ ወደ ሀገር የሚያስገባ እየመሰላቸው ጓዛቸውን ይዘው ሲሄዱ ኤርፖር እያደረሰ የሚመልሳቸው ኤምባሲው አሁንም ህዝቡን ዥዋዥዌ እያጫወተ ነው፡፡ እንዲያውም አንዱ ኤርፖርቱን በነካ እያጫወቱን ነው፡፡ ቤት ንብረታቸውን በትነው እቃቸውን በርካሽ ሸጠው የሚሰጡትን ሰጥተው እወስዳችኋለሁ እያሉ ሶስት ጊዜ ከማመላለስ ውጭ የሰሩት ፋይዳ የለም፡፡

No comments:

Post a Comment