Tuesday, April 7, 2015

የኢትዮጵያ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲ የኢህአዴግን ርዕዮተ-ዓለም በግዳጅ ለሀገር በቀል የሲቪል ሶሳይቲ ከፍተኛ የሥራ መሪዎች በመስጠት ላይ መሆኑ ተሰማ፡

መጋቢት ፳፰(ሃያ ስምንት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ኤጀንሲው በአዳማ ስብስባ እንደሚያካሂድና አንድ የድርጅቱ ከፍተኛ የሥራ መሪ እንዲገኝ በስልክ በተነገራቸው
መሠረት በአዳማ መገኘታቸውን የተናገሩት አንድ የስብሰባው ተሳታፊ ፣ በዚህ ስብሰባ ላይ ምግባረሰናይ ድርጅቶችን አላሰራ ባሉት ሕጎችና አሰራሮች ዙሪያ ምክክር ይደረጋል የሚል ሃሳብ ይዘው በቦታው ቢገኙም የገጠማቸው ግን ፈጽሞ ያላሰቡት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በዚሁ ስብሰባ ላይ ስለሕገመንግስቱ ማለትም የፌዴራል ስርዓት ጠቀሜታ፣ ስለሰብዓዊና ዴሞክራሲዊ መብቶች መከበር፣ ስለብዝሃነት እንዲሁም መንግስትና ሃይማኖት ስለመለያየታቸውና ስለሃይማኖት አክራሪነት ጉዳዮች፣ ስለልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መስመር፣
ስለኪራይ ሰብሳቢነት፣ ስለኒዮሊበራል ሃይላት ኪሳራና የመሳሰሉ የፖለቲካ ትምህርት በአስገዳጅ መልኩ እንዲወስዱ የተደረገ ሲሆን በጉዳዩ ላይ በቡድን እንዲወያዩና ሃሳባቸውንም በቡድን መሪያቸው በኩል እንዲያቀርቡ መደረጉን አስረድተዋል፡፡
የስብሰባው ተሳታፊዎች በሁኔታው ብዙዎቹ ቢበሳጩም በኤጀንሲው የፖለቲካ ሹመኞች ላለመጠመድ ሲሉ በስብሰባው ለመቆየት መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡ «የእነሱ ምርጫ በመድረሱ ብቻ ስንት ሥራ ጥለን የሰለቸ ፖለቲካቸውን ስንጋት ለሶስት ቀናት
መቆየታችን እጅግ አበሳጭቶኛል» ብለዋል የስብስባው ተሳታፊ ምንጫችን፡፡
ኤጀንሲው ስብሰባ ሲጠራ በምን አጀንዳ ላይ ውይይት እንደሚደረግ በደብዳቤ መግለጽ የነበረበት ሲሆን ምናልባት ሰዎች ላይገኙ ይችላሉ በሚል ነገሩን ሚስጢር ሳያደርገው እንዳልቀረ ስብሰባውን የተከታተሉት ምንጫችን አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ኢህአዴግ በምርጫ 97 አስከፊ ሽንፈትን ከቀመሰ በሃላ በድንጋጤ ካወጣቸው አሳሪ ሕጎች አንዱ የሆነው የበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት አዋጅ ቁጥር 621/2001 በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ድርጅቶችና መንግስታት ተቃውሞ ሲገጥመው የቆየና ለበርካታ
ድርጅቶችና መፍረስና መዳከም መንስኤ በመሆኑ በዚህ አዋጅ ላይ አንዳች ማሻሻያ ይኖራል የሚል ተስፋ አድርገው የነበረ ቢሆንም በተቃራኒው ሕጉ የተቀደሰ እንዲሁም «የኒዮሊበራል ሃይላትን ያበሳጨ» መሆኑ ተነግሮአቸው መመለሳቸውን እንዳሳዘናቸው
አስታውቀዋል፡፡
ኤጀንሲው በሁለት ዙር ከመጋቢት 24 እስከ 30/ 2007 ዓ.ም በአዳማ በጠራው ስብሰባ ላይ የተገኙ የኢትዮጵያዊያን ነዋሪዎች በጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት የስራ መሪዎች ፣ በዚህ ስብሰባ ለምን እንዲሳተፉ እንደተፈለገ ግራ ቢገባቸውም ሕገመንግስቱ
የወረቀት ነብር ከመሆን በዘለለ አፈጻጸም ላይ ከፍተኛ ችግር መኖሩን በግልጽ አስቀምጠዋል፡፡
በተለይ ሙስና እና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ከጊዜ ወደጊዜ እየተባባሱ መምጣታቸውን የጠቀሱት እነዚሁ ተወያዮች ከፍተኛ የሀገሪቱ ባለስልጣናት ከችግሩ ጸድተው አርአያ መሆን ስላልቻሉ ከታች ያለውን ሙስናና የኪራይ ሰብሳቢነት እንዲሁም የመልካም
አስተዳደር ችግሮች እንዲቀረፉ ማድረግ እንዳልቻሉና በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ በአሳሳቢ ሁኔታ ላይ እንደምትገኝ አስቀምጠዋል፡፡
ልማትን በተመለከተ በገዥው ፓርቲ ብዙ እንደሚነገርለት ነገር ግን ልማቱ በሰዎች ሕይወት የማይገለጽና  ሰብዓዊ ልማትን ያላካተተ መሆኑን፣ የመንገዶችና የህንጻዎች መሰራት ብቻውን ፋይዳ እንደሌለው ተወያዮቹ ማንሳታቸውን ጉባኤውን የተከታተሉት ምንጫችን
ጠቁመዋል፡፡ በኢትዮጵያ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ጥሰት መኖሩ፣ የሰብዓዊና የዴሞክራሲያዊ መብቶች ባልተከበሩበት ማህበረሰብ ውስጥ ደግሞ ሀገራዊ መግባባት ፈጥሮ በልማት ጉዳይ አንድ አቋም ለመያዝ እንደማይቻል መነገሩን ጠቅሰዋል፡፡
መንግስትና ሃይማኖት የተለያዩ መሆናቸውንና አንዱ በአንዱ ጣልቃ እንደማገባ ሕገመንግስቱ ቢደነግግም መንግስት ግን ሁሉን ለመቆጣጠር ካለው ፍላጎት የተነሳ የመብት ጥያቄ በማንሳታቸው ሲደራደራቸው የነበሩትን የሙስሊም ወገኖች «አክራሪ» የሚል ታፔላ
ተለጥፎላቸው ዘብጥያ መወርወራቸው የመንግስትን ግልጽ ጣልቃ ገብነትና ሕገመንግስታዊ ጥሰት በግልጽ ያሳየ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ገዥው ፓርቲ እና ተቃዋሚዎች አሁንም በጠላትነት መንፈስ እንደሚተያዩና በምንም ጉዳይ የጋራ መግባባት መፍጠር
እንዳልቻሉም የተነሳ ሲሆን ለዚህ ኪሳራ ደግሞ ትልቁን ሃላፊነት የሚወስደው በመንግስትነት 24 ዓመታት የዘለቀው ገዥው ፓርቲ ነው ብለዋል፡፡
ከ200 በላይ ሀገር በቀል የሲቪል ሶሳይቲ አባላት የተገኙበት ሁለተኛው ዙር ስብሰባ እስከመጋቢት 30 ቀን 2007 ዓ.ም እንደሚቀጥል ታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ዜና በቅርቡ ሲሲአርዴ የተባለው መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት በቅርቡ ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በክብር እንግድነት  የተገኙት አቶ  አባዱላ ገመዳ መንግስት ለበጎ አድራጎት ድርጅቶች ቀና አመለካከት እንዳለው ገልጸዋል።  ከገለጻቸው በሁዋላ የማሪ
ስቶፕስ አማካሪ የሆኑት አቶ ጌታቸው በቀለ ” እርስዎ መንግስትና በጎ አድራጎት ማህበራቱ በጋራ እንደሚሰሩ ፣ የበጎ አድራጎት ማህበራት ህግ ከጊዜ ወደ ጊዜ እንደ አስፈላጊነቱ ማስተካከያ እና ማሻሻያ እየተደረገ መሆኑን ይገልጻሉ፣ ነገር ግን ጠ/ሚኒስትሩ የሚናገሩት
እርስዎ ያሉትን የሚንድ ነው፣ የምትናገሩት የግላችሁን አቋም ሳይሆን የመንግስት አቋምን ይመስለኛል።እንዴት ነው የመንግስት ባለስጣናት ሆናችሁ ሁለት የተለያዩ ነገሮችን የምትናገሩት?” በማለት ጠይቀዋል። በእንግሊዝኛ  በተዘጋጀው ውይይት ላይ ንግግራቸውን
በአማርኛ ያቀረቡት አባ ዱላ ገመዳ፣ አማርኛ ፣ ኦሮምኛ ፣ ትግርኛና እንግሊዝኛ እንደሚናገሩ ይሁን እንጅ በቋንቋቸው መናገራቸው ስለሚያስደስታቸው በአማርኛ ለመናገር መምረጣቸውን ለተነሳው ጥያቄ መልስ ሰጥተዋል።
አቶ አባዱላ ”  ብዙ ችግሮችን የሚፈጥሩ አምነስቲ፣ ሂውማን ራይትስ ወች የሚባሉት ድርጅቶች በእኛና በሩዋንዳ ላይ የማይሉት ነገር የለም። እኛ የትልልቆቹ አገራት ፍላጎት ማስፈጸሚያ አንሆንም ስንል የማይሉት ነገር የለም። እነሱ መንግስት መሆን ስለሚፈልጉ ነው።
እኛ ራሳችንን ከቻልን ብዙ ስራ የሚያጣ ብዙ ቢሮ የሚዘጋበት አለ። ጠ/ሚኒስትሩ የእነሱ አላማ አስፈጻሚ አትሁኑ ነው ብለው የመከሩት። አንድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ለዚች አገር ምንም አይደለም። ከዚህ የተሻለ ደረጃ ላይ ያለች አገር ነው ያለችን። እናም የእነሱ አላማ
ማስፈጸሚያ እንዳትሆኑ ተጠንቀቁ ” ሲሉ በበጎ አድራጎት ላይ የተሰማሩትን አስጠንቅቀዋል።

Source: ethsat.com

No comments:

Post a Comment