Tuesday, January 26, 2016

ገዢው ፓርቲ የህዝብን ተቃውሞ ለማብረድ የሚወስደው እርምጃ የይስሙላ ነው ሲሉ አባላቱ ገለጹ

ገዥው ፓርቲ ኢህአዴግ ከሕዝቡ እየደረሰበት ያለውን ተቃውሞ ለማርገብ ከክልል አስከ ቀበሌ ባሉት መዋቅሮቹ
አባሎቹን ማባረር ቢጀምርም ከፍተኛ አመራሩን ያላካተተ መሆኑ ከወዲሁ በራሱ አባሎች ተቃውሞ እያስከተለበት ነው።
ኢህአዴግ በነሀሴ ወር 2007 ዓ.ም በመቀሌ ከተማ ባካሄደው 10ኛው ድርጅታዊ ጉባዔው የመልካም አስተዳደር
ችግሮች ከፍተኛ ደረጃ መድረሳቸውን በማመን የማጥራት ሥራው ከከፍተኛ አመራሩ ጀምሮ እንዲካሄድ ውሳኔ ያሳለፈ ይሁን
እንጂ ከፍተኛ አመራር ውስጥ በሙስና የሚጠረጠሩት ነባሮቹ የህወሀት አመራሮች ከመሆናቸው ጋር ተያይዞ ቁርጠኛ
እርምጃ ለመውሰድ ሳይችል ቀርቶአል፡፡
ግንባሩ ሕዝቡን በመልካም አስተዳደር ችግሮች ላይ እርምጃ እየወሰድኩኝ ነው ለማለት ያህል የመልካም አስተዳደር
ንቅናቄ በሚል ትልልቆቹን ሙሰኞች በጉያው አቅፎ የወረዳና ቀበሌ አመራሮችን ወደማባረር ማዘንበሉ የግንባሩ ውሳኔ
መተግበር እንደማይችል ፍንጭ ያሳየበት ተጨባጭ ክስተት ነው ሲሉ አባሎቹ እየተቹት ነው።
ሰሞኑን በአማራ ክልል ለድርቅ ተጎጆዎች የመጣ የእርዳታ እህል ለግል ጥቅማቸው አውለዋል የተባሉ፣ በመሬት ወረራ
የተጠረጠሩ፣ በመልካም አስተዳደር ችግር ፈጥረዋል የተባሉ ከክልል እስከ ቀበሌ ያሉ አመራሮችና 45 የፖሊስ
አባላት የተባረሩ መሆኑን በመንግስት መገናኛ ብዙሃን የተገለጸ ሲሆን፣ በተመሳሳይ ሁኔታ በትግራይ፣ በደቡብ፣
በኦሮሚያና በሌሎችም ክልሎች የማባረር የዘመቻ ስራው የቀጠለ መሆኑ ታውቆአል፡፡ ሆኖም የካቢኔ አባላት የሆኑ
በሚኒስትር፣ በኮምሽነር፣ በዋና ዳይሬክተርና በጠ/ሚኒስትሩ አማካሪነት ደረጃ የተቀመጡ ሙሰኞች ምንም ሳይነኩ
ይባስኑም በእነሱ አመራር ሰጪነት እየተካሄደ ያለው የማባረር ዘመቻ ለኢህአዴግ አባከላት ራሱ አስቂኝ መሆኑንና
ጉዳዩ ውስጣዊ ቅራኔን በመፍጠር ላይ መሆኑን የግንባሩ ምንጮቻንን ገልጸዋል።
አንዳንድ የኢህአዴግ አባላት የታችኛው አመራር ህገወጥነትንና ሌብነትን የተማረው ከከፍተኛዎቹ ነው በማለት
የማጥራት ስራው ግልጽ በሆነ መንገድ ከከፍተኛ አመራሮች ካልጀመረ በስተቀር በየወረዳውና ቀበሌው እየዞሩ ሰዎች
ከስራ ማፈናቀሉ ብቻውን ለውጥ አያመጣም በማለት በግልጽ መሞገት መጀራቸውን አባላት ተናግሯል።
ጠ/ሚኒስትር አቶ ሃይለማርያም የመልካም አስተዳደር ችግርን በተመለከተ ከከፍተኛ አመራሮቻቸው ጋር በቅርቡ
ባደረጉት ውይይት በሚኒስትር ደረጃ ያሉ ከፍተኛ አመራሩ ጭምር በኔትወርክ የተሳሰረና በደላላ የሚመራ መሆኑን
ተናግረው ነበር።
Source : http://ethsat.com/amharic/%E1%8C%88%E1%8B%A2%E1%8B%8D-%E1%8D%93%E1%88%AD%E1%89%B2-%E1%8B%A8%E1%88%85%E1%8B%9D%E1%89%A5%E1%8A%95-%E1%89%B0%E1%89%83%E1%8B%8D%E1%88%9E-%E1%88%88%E1%88%9B%E1%89%A5%E1%88%A8%E1%8B%B5-%E1%8B%A8/

No comments:

Post a Comment