Tuesday, October 27, 2015

የመንግሥት ኮምኒኬሽን ጽ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት አቶ ሽመልስ ከማል ከኃላፊነታቸው ተነሱ


ጥቅምት ፲፮ (አስራ ስድስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-አቶ ሽመልስ ፣ አቶ በረከት ስምኦን ከኮምኒኬሽን ሚኒስትርነት ተነስተው በአቶ ሬድዋን ሁሴን ከተተኩበት ካለፉት ሁለት ዓመት ተኩል ወዲህ ከአቶ ሬድዋን ጋር መስማማት ባለመቻላቸው በስራ ገበታቸው ላይ የሚገኙት አልፎ አልፎ ነበር፡፡ የሁለቱ ሚኒስትሮች አለመግባባት በኢሳት ከቀረበ በኃላ ችግር የለብንም ለማለት ለአንድ ቀን አብረው መግለጫ በመስጠት ጎን ለጎን ተቀምጠው ከታዩ ወዲህ ደግመው እንኳን አብረው መታየት አልቻሉም፡፡
የአቶ ሬድዋን እና የአቶ ሽመልስ አለመግባባት ትክክለኛ ምክንያት ባይታወቅም የቅርብ ባልደረቦቻቸው እንደሚናገሩት ከቡድንተኝነት ጋር የተያያዘ ነው፡፡
የአቶ ሽመልስ ውግንና ከእነአቶ በረከት ስምኦን ጋር መሆኑ በእነአቶ ሬድዋን ባለመወደዱ፣ ሰበብ አስባብ እየፈለጉ በመተቸት ግለሰቡን ከአጠገባቸው ዞር እንዲሉ ማድረጋቸው በባልደረቦቻቸው ይነገራል፡፡ በአቶ ሬድዋን በኩል አቶ ሽመልስን በተመለከተ ተደጋግሞ የሚነሳው ሥራውን በአግባቡ አይሰራም፣ ቢሮ አይገኝም የሚል ቢሆንም ዋንኛ ምክንያት ግን የፖለቲካ ቡድንተኝነት የፈጠረው መሆኑን ባልደረቦቻቸው ይናገራሉ።
በአሁኑ ሰዓት አቶ ሽመልስ የት እንደተመደቡ ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ያልታወቀ ሲሆን በቀጣይ ቀናት ግን አንድ ቦታ በአማካሪነትም ቢሆን መሾማቸው የማይቀር መሆኑን ምንጮቹ ገምተዋል፡፡
አቶ ሽመልስ ከማል የ1997ቱን ታሪካዊ ምርጫ ተከትሎ በተለይ የቅንጅት ተከሳሾችን ጉዳይ በአቃቤ ሕግነት በመያዝና በመምራት ከዚህ ቀደም በስራ ይተዋወቁዋቸው የነበሩ የቅርብ ጓደኞቻቸውን ጭምር የጥቅም ግጭት በሚያስከትል መልኩ ሐሰተኛ መረጃዎችንና ምስክሮችን በማዘጋጀት ከባድ ቅጣት እንዲጣልባቸው የራሳቸውን ሚና የተወጡ የኢህአዴግ ባለውለታ ናቸው፡፡
አቶ ሽመልስን የተኩት የብአዴን ታጋይና ማዕከላዊ ኮምቴ አባል የሆኑት ወ/ሮ ፍሬሕይወት አያሌው ሲሆኑ ፣ ወደ ጠ/ሚኒስትር ቢሮ የተዛወሩትን የኦህዴዱ አቶ እውነቱ ደበላን የተኩት ደግሞ የኦህዴድ አባልዋ ወ/ሮ ብርቅነሽ ብሩ ናቸው፡፡
Source:: Ethsat

No comments:

Post a Comment