Monday, August 31, 2015

ቤኒሻንጉል ክልል በሚኖሩ የአማራ ተወላጆች ላይ ግድያ ተፈጸመባቸው


ኢሳት ዜና (ነሐሴ 25, 2015)
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሚገኙ የአማራ ተወላጆች ላይ የተቀነባበረ ጥቃት መሰንዘሩን የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት ገለጹ። ባለፈው ሚያዚያ ወር መጨረሻ ተፈጸመ በተባለው በዚሁ ጥቃት፣ ከ80 በላይ ሰዎች መገደላቸውንና በአንድ ቀበሌ ውስጥ የሚገኙ አማሮች ሙሉ በሙሉ የጥቃቱ ሰለባ መሆናቸውን ዕማኞች ለኢሳት ገልጸዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወንበራ ወረዳ መልካ ቀበሌ ከሶስት ወራት በፊት በተፈጸመው በዚሁ ጥቃት 84 ሰዎች መገደላቸውን የገለጹት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ግድያውም በጦር መሳሪያና በስለት ጭምር የታገዘ መሆኑን አስረድተዋል። ለቀናት አማሮች የሚደርስላቸው በማጣታቸው የተረፉት ንብረታቸውን ጥለው መሸሻቸውን ገልጸዋል።
ሚያዚያ 27 እና 28 ለሁለት ቀናት በወንበራ ወረዳ መልካ ቀበሌ ለቀጠለው ጥቃት መነሻው አንድ የአካባቢው ተወላጅ ባልታወቁ ሰዎች ተገደሎ መገኘቱ እንደሆነም ተመልክቷል።
በአማሮች ላይ በአካባቢው ባለስልጣናት ግፊትና ድጋፍ ለተቀነባበረውና ለቀጠለው ጥቃት የሚደርስ አካል በመታጣቱ፣ ሰለባዎቹ ለቀናት አደጋውን ሲጋፈጡ መቆየታቸውንም መረዳት ተችሏል።
ኢሳት ያነጋገራቸው ሁለት የአካባቢው ነዋሪዎች እንደገለጹት የሟቾቹ አስከሬን የተሰበሰበው የመከላከያ ሰራዊት አባላት ከቀናት በኋላ ወደስፍራው ሲደርሱ ነው።
ጥቃቱን በማድረስ የተጠረጠሩ 10 ያህል ሰዎች የተያዙ ቢሆንም፣ ድርጊቱን በማቀነባበርና በመምራት ተሳታፊ የሆኑ ባለስልጣናት አለመጠየቃቸውን መረዳት ተችሏል።

No comments:

Post a Comment