Tuesday, August 25, 2015

የደቡብ ክልል አመራሮች እርስ በርስ እየተወነጃጀሉ ነው


ነኅሴ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በታደለ ቱፋ የተጻፈውን የጋሞን ህዝብ ማንነት የሚያንቋሽሸውን መጽሃፍ ፣ አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ የሚመሩት የደቡብ ህዝቦች ዲሞክራሲያዊ ድርጅት ከፍተኛ አመራሮች የገንዘብ ደጋፍ በማድረግ አስጽፈውታል በሚል ምክንያት ፣ በአርባምንጭና በተለያዩ የጋሞ ወረዳዎች የተቃውሞ ሰለፎች መደረጋቸውን ተከትሎ፣ በከፍተኛ አመራሩ እና በታች አመራሩ መካከል ያለው አለመግባባት ይፋ ሆኗል።
ለኢሳት የደረሰው የድምጽ ማስረጃ ከመጽሃፉ ጋር በተያያዘ ቀደም ብሎ ኢሳት በአመራሩ መካካል ልዩነት መፈጠሩን በተመለከተ ያቀረበውን ዘገባ የሚያረጋገጥ ነው። የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ ደሴ ዳልኬ፣ የጋሞ ጎፋ የዞንና የወረዳ አመራሮች፣ የደኢህዴን ባለስልጣናት እጃቸው አለበት በሚል የሚያናፍሱት ወሬ ትክክል አይደለም በማለት፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች ጥፋታቸውን እንዲቀበሉ ጫና አድርገዋል። የወረዳ አመራሮች በተለይም የጨንጫ እና የአርባምንጭ የወረዳ አመራሮች ሂሳቸውን ወይም ጥፋታቸውን ለመቀበል ዝግጁ ካልሆኑ፣ የጥገኞች አስተሳሰብ አራማጆች ተብለው እንደሚፈረጁ በፕሬዚዳንቱ ተነግራቸዋል።
የወረዳ አመራሮች ከመጽሃፉ ጋር በተያያዘ ” ህዝቡ ከአመራሩ ጋር ሆድና ጀርባ ሆኗል” ቢሉም፣ የክልል መሪዎች ” ሊቀበሉት ፈቃደኞች አልሆኑም።
ፕሬዚዳንቱ መጽሃፉን ደኢህዴን እንደላስጻፈውና እንዲያውም ሁሉም የድርጅቱ መሪዎች ደራሲውን ማውገዛቸውን ገልጸዋል። ምንም እንኳ ደራሲው ታስሮ በዋስ የተፈታ ቢሆንም፣ ፕሬዚዳንቱ ግለሰቡ ተመልሶ እንዲታሰርና ፍርድ ቤት የዋስትና መብቱን ጠብቆ የሚፈታው ቢሆን እንኳ፣ እርሳቸው እንደማይፈቱት በመናገር፣ ኢህአዴግ ባለስልጣናት ከህግ በላይ ወይም ከፍርድ ቤት በላይ መሆናቸውን አስመስከረዋል፡፡
ይህ አንድ መጽሃፍ እርስ በርስ እንድንጠራጠርና እንዳንተማመን ካደረገን፣ እስከዛሬ አብረን የተጓዝነው ጉዞ የውሸት ነበር ያሉት መሪው፣ መጽሀፉ የድርጅቱን መዋቅር እንዲፈትሹ እና የደኢህዴንን የድርጅት ጥንካሬና በአመራሩ መካካል ያለውን መተማመንና መደጋገፍ እንደገና እንዲመረምሩ እንዳስገደዳቸው ገልጸዋል።
በሌላ በኩል ዶ/ር ካሱ ኢላላ ከአመራር ቦታ ላይ ሲነሱ ዶ/ር ሽፈራው ደግሞ ከኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚነት ተነሱ
የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት /ደኢህዴን/ ጉባኤ ለቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት የድርጅቱ የስራ
አስፈጻሚና የማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትን የመረጠ ሲሆን፣ በሕዝበ ሙስሊሙ ጠላት ናቸው የሚባሉትን ዶ/ር
ሽፈራው ተ/ማርያም ከኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚነት አሰናብቶ የድርጅቱ ስራ አስፈጻሚ አድርጓቸዋል። ዶ/ር ካሱ ኢላላን በመተካካት ስም ሸኝቶአል፡፡
ጉባዔው 65 አባላት በማዕከላዊ ኮምቴ አባልነት የመረጠ ሲሆን ከእነዚህ መካከል ዘጠኝ ያህሉ ማለትም አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ፣ ደሴ ዳልኬ ፣ ተስፋዬ በልጂጌ ፣ ሲራጅ ፈጌሳ ፣ ሬድዋን ሁሴን ፣ መኩሪያ ሀይሌ ፣ መለሰ አለሙ ፣ ተክለወልድ አጥናፉ እና ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም የድርጅቱ ስራ አስፈጻሚዎች ሆነዋል።

No comments:

Post a Comment