Thursday, April 16, 2015

(የቡና ቁርስ) በዚህ ሳምንት የተማርናቸው ሦስት ነገሮች * ኬንያም ኢትዮጵያም ሽብርተኝነት ላይ ሚዛን ስተዋል * ዶናልድ ሌቪን የኔታ ናቸው * ድምጻችን ይሰማ ብርቱ ነው


1ኛ) ኬንያም ኢትዮጵያም ሽብርተኝነት ላይ ሚዛን ስተዋል 
ከሁለት ዓመት በፊት ዘ-ኢኮኖሚስት መጽሔት ጎረቤታሞቹ ኢትዮጵያ እና ኬንያ በሚከተሏቸው የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ አስተዳደር ሞዴሎች መካከል ያለውን ልዩነት የሚገልጽ ጽሑፍ አስነብቦን ነበር። ጽሑፉ የሚጀምረው ሁለት የድንበር ከተሞችን በማነጻጸር ነበር፤ መተማን እና የኬንያ ሞያሌን። በመተማ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለመግባት ጥብቅ በኾነ የፍተሻ ሂደት ውስጥ ማለፍ ግድ ይላል። ድንበር ጠባቂዎቹ የተጓዦች ፓስፖርቶችን በእጅ ጽሑፍ ከተጻፈ ወደ ኢትዮጵያ እንዳይገቡ የተከለከሉ ሰዎችን ስም ዝርዝር ከያዘ ዶክመንት ጋራ ያመሳክራሉ። ፓስፖርቶቹ የሐሰት እንዳልኾኑ በጥንቃቄ ይመረምራሉ፤ ግልምጥምጥ እያደረጉ እና ኮስተርተር እያሉ ጥያቄ ይጠይቃሉ። በሞያሌ በኩል ወደ ኬንያ ለመግባት ግን ይህ ሁሉ ጣጣ የለም። የደንህንነት መኮንኖቹ ፓስፖርት ሲመለከቱ ፈታ፣ ዘና ብለው ነው። ጥበቃው ልል ከመኾኑ የተነሳ “የድንበር ፍተሻ ሳይኾን የእንኳን ደህና መጡ አቀባበል ይመስላል” ይላል ዘ-ኢኮኖሚስት። የኢትዮጵያ የአስተዳደር ሞዴል መተማን ይመስላል፤ መንግሥት ሁሉ አወቅ የኾነበት እና ከዳር እስከ ዳር ሥልጣኑንና ቁጥጥሩን ያረጋገጠበት። የኬንያ መንግሥት በተቃራኒው የቁጥጥር ድክመት ያለበት እና ክፍትነት የሚታይበት ነው።
BEN CURTIS, FILE — AP Photo Read more here: http://www.adn.com/2013/10/10/3119796/africa-vs-icc-quotes-on-court.html#storylink=cpy
BEN CURTIS, FILE — AP Photo
Read more here: http://www.adn.com/2013/10/10/3119796/africa-vs-icc-quotes-on-court.html#storylink=cpy
ባለፈው ሳምንት በጋሪሳ 147 ሰዎች ያለቁበትን የሽብር ጥቃት ተከትሎ በእነዚህ ሁለት ተቃራኒ ሞዴሎች ጉዳይ ክርክር ተጀምሯል። በኬንያ እንዲህ ዐይነት የሽብር ጥቃት ሲፈጸም የመጀመርያው አይደለም። በተቃራኒው በኢትዮጵያ ከ1999 ዓ.ም በኋላ መጠነ ሰፊ የሽብር ጥቃት አልተፈጸመም። አልሸባብ ሁለቱንም አገሮች (በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያን) እንደ ከባድ ጠላት ይመለከታል። ነገር ግን የኬንያ ስኬቱን በኢትዮጵያ ሊደግመው አልቻለም። ይህን ያስተዋሉ አንዳንድ ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያን የአስተዳደር ሞዴል አንቆለጳጵሰውታል። እንዲህ ያሉ ክስተቶችን ተገን አድርገው ቋጥኝ የሚያካክሉ መደምደሚያዎች ላይ የሚደርሱ ሙግቶችን እና ትንተናዎች (ad hoc reasoning) ፋይዳ አነስተኛ ነው። ሲስተሞችን እና ሞዴሎችን በርትዕ እንዳንማር ያደርጉናል። ትልቁን ሥዕል እንዳንመለከት ዐይኖቻችንን ይጋርዷቸዋል። ይልቁንስ የሞዴሎችን ብቃት ለማወቅ መለኪያዎችን አውጥቶ መገምገም የተሻለ መንገድ ነው።
የፖለቲካ ፈላስፋዋ ሴይላ ቤን ሃቢብ ውስብስብ የፖለቲካ ማኅበረሰቦች አራት እሴቶች እንዳሏቸው ያስቀምጣሉ፤ ሌጂትሜሲ፣ የኢኮኖሚ ዋስትና፣ ደኅንነት እና አመክኗዊ የጋራ ማንነት። እነዚህ ግቦች በብዙኀኑ የፖለቲካ ማኅበረሰቦች አባላት የሚደገፉ ናቸው፤ በትርጉማቸው እና በይዘታቸው ላይ በየማኅበረሰቡ ጠንካራ ሙግቶች እና ያለ መስማማቶች ቢኖሩም። እነዚህ ግቦች እርስ በእርሳቸው የተወሳሰበ መስተጋብር አላቸው። አንዱን በተትረፈረፈ ኹኔታ ማግኘት ሌላውን ሊያሳጣ ይችላል። ለምሳሌ፦ ሌጂትሜሲን ለማምጣት እጅግ ክፍትና ነጻ የኾነ ሥርዐት ፈጥረን ደህንነትን አደጋ ላይ ልንጥል እንችላለን። የኢኮኖሚ ዋስትናን ለመጨመር ደግሞ የሰዎች ነጻነት ላይ ከመጠን ያለፈ ገደብ እናስቀምጥ ይኾናል። የጋራ ማንነታችንን ለማጠናከር ውህዳንን (minorities) እንጨቁናለን። የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሞዴሎች ብስለት እና ብቃት የሚለካው እነዚህን አራት እሴቶች አመዛዝኖ በማቅረብ ችሎታቸው ነው። በእነዚህ መለኪያዎች እንደ ኢትዮጵያ ያለ እጅግ ጣልቃ ገብና ሁሉን ዐወቅ መንግሥት በሳል ነው ለማለት ያስቸግረናል። ሕዝቡን መንግሥታዊ ካልኾነ ሽብር ለመጠበቅ ቢችልም፤ ይህን የሚያደርገው ሌጂትሜሲን እና የጋራ ማንነትን አደጋ ላይ በመጣል ነው። ለምሳሌ በ1999 ዓ.ም በኦጋዴን የተፈጠረውን ክስተት እናንሳ። የኦጋዴን ብሔራዊ ነጻነት ግንባር ታጋዮች በቻይና የነዳጅ ኩባንያ ላይ ጥቃት ፈጽመው 74 ሠራተኞችን ገደሉ፤ ብዙ ንብረት አወደሙ። የኢትዮጵያ መንግሥት በአጸፋው ለሦስት ዓመታት ሳያሰልስ የቀጠለ መሬት አንዳጅ፤ ጅምላ ጨራሽ ወታደራዊ እርምጃ ወሰደ። በርካታ የኦጋዴን ነዋሪዎች ተገደሉ፤ ተገረፉ፣ ተሰቃዩ፣ ቀያቸውን ለቀው ተሰደዱ። ይህ ጥቃት ኦብነግን ቢያሽመደምደውም የኦጋዴን ነዋሪዎችን መብቶች ክፉኛ የጣሰ እና ኢትዮጵያዊ ማንነታቸውን የበለጠ እንዲጠይቁ ያደረገ ነበር። አራቱን እሴቶች የሚያመዛዝን ሳይኾን ወደ አንዱ እሴት በእጅጉ ያዘነበለ ጥቃት ነበር። የተከፈለው ዋጋ የፖለቲካ ማኅበረሰባችንን አናግቷል። ኬንያ ከኢትዮጵያ በተቃራኒ ጫፍ ላይ ያለ የራሷ የኾነ አመዛዝኖ የማቅረብ ችግር አለባት። ለብሔራዊ ደህንነት የምትሰጠው ዋጋና ክብር አነስተኛ ነው። በኬንያ ላይ ጣታቸውን የቀሰሩ ኢትዮጵያውያን ይህን በሚገባ አብራርተውታል። ችግሩ ሦስቱ ጣቶቻቸው ወደራሳቸው እንደሚጠቁሙ መዘንጋታቸው ነው።
2ኛ) ዶናልድ ሌቪን የኔታ ናቸው
ታላቁ አሜሪካዊ የፖለቲካ ፈላስፋ ጆን ሮውልስ ከወጥ ሥራዎቹ በተጨማሪ በአንድ ነገር ይታወቃል፤ በየኔታነት (mentorship)። ለተማሪዎቹ የቅርብ ጓደኛ ኾኖ ሥራቸውን መከታተል እና ማበረታታት እንደ ምሁራዊ ግዴታው ይመለከት ነበር። ይህ ጠባዩ በርካታ ድንቅ ፈላስፎችን እንዲፈጥር ከማስቻሉም በተጨማሪ ተክለ ሰብእናውን እና ምሁራዊ ብቃቱን የሚያበስሩ ደቀ መዛሙርት እንዲያፈራ አድርጎታል። የምሁራን ስኬት በሥራቸው ብቃት ብቻ ሳይኾን በሌሎች ምሁራን ዘንድ ባላቸው ማኅበራዊ ካፒታል (social capital) ይወሰናል። ባለፈው ሳምንት በሞት የተለዩን የኢትዮጵያ ጥናቶች ታላቅ ሊቅ አሜሪካዊው ሶሲዮሎጂስት ዶናልድ ሌቪን ይህን እውነታ በሚገባ የተረዱ ነበሩ።
Oromo Narrative: Professor Donald Levineፕሮፌሰር ሌቪን በኢትዮጵያ ላይ የጻፏቸው ሁለት ታላላቅ መጻሕፍት ከታተሙ ቢያንስ አርባ ዓመታት አስቆጥረዋል። ከዚያ በኋላ የእርሳቸውን ሥራዎች የሚያፈርሱ እና በጥብቅ የሚሄይሱ ጥናቶች ታትመዋል። የተሻሉ ቲዮሪዎች እና ኢምፔሪካል ግኝቶች ተከትለዋል፤ የኢትዮጵያ ጥናቶች አድገዋል፤ ተመንድገዋል። መጻሕፎቻቸው በብዙ ወጣት ምሁራን ሥራዎች ውስጥ ቢጠቀሱም ሌቪኒዝምን አልፈጠሩም። በተጨማሪም ፕሮፌሰር ሌቪን ከምሁራዊ ሥራቸው አልፈው በኢትዮጵያ ፖለቲካ መጀመርያ ንጉሡን የሚቃወሙ ኀይሎችን በመርዳት በኋላም የቅንጅት ታሳሪዎች እና ኢሕአዴግን ለማደራደር በሽማግሌነት ያደረጓቸው ጥረቶች ያልተሳኩ ነበሩ። በተለያዩ ጊዜያት በኢትዮጵያ የፖለቲካ ኢኮኖሚ ላይ የጻፏቸው መጣጥፎች ብዙም ተቀባይነት አላገኙም፤ እንዲያውም ከአንዳንዶች ጠንካራ ትችት ተሰንዝሮባቸዋል። ይኹንና በዶናልድ ሌቪን ሞት ተቺዎቻቸውን ጨምሮ በርካታ ኢትዮጵያውያን ምሁራን ከልብ የመነጨ ሐዘናቸውን ሲገልጹ ሰንብተዋል። እነዚህ ምሁራን የሦስት ትውልድ አባላት ናቸው። አብዛኞቹ በሐዘን መግለጫቸው ከሌቪን አካዳሚያዊ ሥራዎች በተጨማሪ ከፕሮፌሰሩ ጋራ የነበራቸውን የጓደኝነት እና የተማሪ -መምህር ግንኙነት አንስተዋል። ሌቪን ከወጣት እስከ አዛውንት ከምሁራን ጋራ በመቀራረብ፣ ሳይታክቱ የደብዳቤ እና የኢ-ሜይል ልውውጦችን በማድረግ የድጋፍ ደብዳቤዎችን በመጻፍ፣ በአካዳሚያዊ ኮንፈረንሶች እና ሌሎች የትምህርት አውድማዎች በመገኘት ተፈንክቶና ተዘርዝሮ የማያልቅ ማኅበራዊ ካፒታል አዳብረዋል። ይህ ካፒታል የፖለቲካ ስህተት ሲሠሩ ሳይቀር ስማቸውን ከሚያበሻቅጥ ጥቃት እና ዝቅ አድርጎ ከሚያይ አስተያየት ጠብቋቸዋል። የኔታ ሊበን አፈር ይቅላለቸው።
3ኛ) ድምጻችን ይሰማ ብርቱ ነው
በአምባገነን ሥርዐቶች መንግሥታት ላይ ግፊት የሚያደርጉ ማኅበራዊ ንቅናቄዎች ዕድሜ እጅግ አጭር ነው። ከምሥረታቸው አንስቶ የማኅበራዊ ድርጊት ችግሮች (collective action problems) ይገጥሟቸዋል። መንግሥት ሰርጎ ገቦችን ያዘልቅባቸዋል፤ መሪዎቻቸው እና አባሎቻቸው ይታሠራሉ፤ ተለጣፊ ቡድኖች ይፈጠሩባቸዋል። በአጠቃላይ በእነዚህ ንቅናቄዎች ውስጥ የመሳተፍ ዋጋ (cost of participation) ይሰቀላል። ብዙዎች ተስፋ ቆርጠው ንቅናቄውን እንዲተዉ ያደርጋል፤ ዋጋ ሳይከፍሉ ስኬት መካፈል የሚፈልጉ ሰዎችን (free riders) ያበራክታል። ማኅበራዊ ንቅናቄዎች ከተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች በበለጠ ለእንደዚህ ዐይነቶቹ የአምባገነን መንግሥት ጥቃቶች የሚጋለጡባቸው የተለያዩ ምክንያቶች አሉ። ማኅበራዊ ንቅናቄዎች የአይዲዮሎጂ ጥራት እና ጥልቀት ይጎድላቸዋል፤ ከፖለቲካ ፓርቲዎች የበለጠ ሰፊ እና ልል ናቸው፤ አባላቶቻቸውን የሚያጣሩበት ወንፊት ዘርዘር ያለ ነው። ይኼን ሁሉ ግምት ውስጥ ስናስገባ ከአራት ዓመታት በላይ የቆየው የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ድማጻችን ይሰማ ንቅናቄ ቀጣይነት ያስገርማል።
yisemaድምጻችን ይሰማ እንደ ብዙ ማኅበራዊ ንቅናቄዎች ሁሉ ልል ነው። በአባላቱ መካከል የስትራቴጂ፣ የታክቲክ እና አንዳንዴም የአይዲዮሎጂ ልዩነት ይታያል። ለምሳሌ፦ አንዳንዶቹ ሌማት ጠያቂዎች (maximalist) ሲኾኑ ሌሎቹ ደግሞ ኩርማን ጠያቂዎች (minimalist) ናቸው። በርካታ አባላት ጥያቄው ከሕገ መንግሥት እና ከአጠቃላይ የሰብአዊ መብት ጽንሰ ሐሳብ ጋር ብቻ የተገናኘ ዓለማዊ (secular) እንዲኾን ይፈልጋሉ። አንዳንዶቹ ደግሞ ንቅናቄው ሃይማኖታዊነቱን እንዲያስረግጥ ይሻሉ። ጥቂት የማይባሉ አባላት ደግሞ መንግሥት በሃይማኖት ላይ ያለውን ጣልቃ ገብነት ካቆመ አጨብጭበው ወደ ቤታቸው መመለስ ይፈልጋሉ፤ ከእነርሱ በተቃራኒ አንድ ጥያቄ ሲመለስ ሌላ እየጨመሩ ማኅበራዊ ንቅናቄው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ በቀጣይነት መሳተፍ እንዳለበት የሚያምኑ አሉ። ከሌሎች የፖለቲካ እና ማኅበራዊ ንቅናቄዎች ጋር መሥራት በሚፈልጉና በማይፈልጉ መካከል ልዩነት አለ። እንደዚህ ዐይነት የውስጥ ሙግቶች እንደ ድክመት ሳይኾን የማኅበራዊ ንቅናቄ ባሕርያት (features) መታየት አለባቸው። መንግሥት ልዩነቶቹን በመጠቀም ንቅናቄውን ለመከፋፈል ሞክሯል። በዚያ ስላልተሳካለት ቀጥተኛ የጭፍለቃ ርምጃዎችን ወስዷል። ይኹንና በዚህ ሳምንት በአውሮፓ እና በአሜሪካ ያንሰራራው እንቅስቃሴ እንደሚያሳየው ንቅናቄው ቢዳከምም አልከሰመም። ከ1966ቱ አብዮት በኋላ ተፈጥረው ለረጅም ጊዜ የቆዩ ማኅበራዊ ንቅናቄዎችን ታሪክ ስናጠና እጅግ በርካቶቹ በነጻ አውጪ ግንባሮች ጥላ ሥር የተሰበሰቡ ኾነው እናገኛቸዋለን። ድምጻችን ይሰማ ከእነዚህ የተለየ ነው። ድምጻችን ይሰማ ያለ ነጻ አውጪ ግንባሮች እና ፖለቲካ ፓርቲዎች ሞግዚትነት በአንጻራዊ ብቻውን ቆሞ ለረዥም ጊዜ መቆየቱ ልዩ ያደርገዋል።

No comments:

Post a Comment