Wednesday, October 19, 2016

Eskinder, Woubshet, Temesgen couldn't appear as defense witnesses

"እስክንድር ነጋ በማረሚያ ቤት ታራሚዎችን ለረብሻ እና ብጥብጥ እያነሳሳ ይገኛል። ...ለፖሊስ የእጀባ ሥራም አደጋ ይፈጥራል። በዚህ የተቸገርን መሆኑን ፍርድ ቤቱ ይረዳልን"
- የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ደብዳቤ

"የዝዋይ ማረሚያ ቤት የትራንስፖርት ችግር ገጥሞት ነው። ታራሚዎችን የሚያመላልሰው መኪና ተበላሽቶ ለጥገና አዲስ አበባ መጥቶ ስላልተመልሰ ተመስገን ደሳለኝንና ውብሸት ታዬን በቀጣይ ቀጠሮ እንድናቀርብ ከይቅርታ ጋር እንጠይቃለን"
- የዝዋይ ማረሚያ ቤት ደብዳቤ

የቃሊቲ ማረሚያ ቤት በቂ ምክንያት ባለማቅረቡ እስክንድር ነጋን በቀጣይ ቀጠሮ በቂ አጃቢ ተመድቦለት በቀጣይ ቀጠሮ ይቅረብ"
- የችሎት ዳኛ
--------
ዛሬ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ 2ኛ ወንጀል ችሎት እኔና አምሳሉ ገ/ኪዳን ቀሪ የመከላከያ ምስክሮችን ለማድመጥ ቀጠሮ ነበረን። ሆኖም በተለያዩ ምክንያቶች የተነሳ ምስክሮችን ማድመጥ ሳይቻል ቀርቶ ለታህሳስ 20 ቀን 2009 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።

በዛሬው ቀጠሮ፣ ጠበቃ አምሃ መኮንን 2ኛ ተከሳሽ አምሳሉ ገ/ኪዳን እግሩን ሪህ ስላመመውና በዚህም የተነሳ ከክፍለ-ሀገር መምጣት አለመቻሉን፣ ነገር ግን በቀጣይ ቀጠሮ የሃኪም ማስረጃ እንደሚያቀርብ በመግለጽ ነበር ችሎቱ የተጀመረው።

ከሳሽ አቃቤ ህግም፣ ዳኛው በችሎት ከተሰየሙ በኋላ በጣም ዘግይቶ ነበር የተገኘው። በዚህ መሃል አንዲት የማረሚያ ቤት ፖሊስ ለዳኛው ሁለት ደብዳቤዎችን ሰጠች። የችሎቱ ዳኛም ደብዳቤዎቹን አይተው ማንበብ ጀመሩ።

የመጀመሪያው ደብዳቤም አጠቃላይ ይዘት "ለ1ኛ ተከሳሽ መከላከያ ምስክር የሆኑት ተመስገን ደሳለኝና ውብሸት ታዬ (ጋዜጠኞች) በዝዋይ ማረሚያ ቤት ይገኛሉ። ማረሚያ ቤቱ የትራንስፖርት ችግር ገጥሞታል። ታራሚዎችን ለተለያዩ ጉዳዮች የሚያመላልሰው መኪና ተበላሽቶ ለጥገና ከሄደበት አዲስ አበባ ስላልተመለሰ ሁለቱን ምስክሮች በቀጣይ ቀጠሮ ማቅረብ እንድንችል ከይቅርታ ጋር እንጠይቃለን" የሚል ነው።

2ኛ ደብዳቤ ደግሞ ከአዲስ አበባ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የተጻፈ ሲሆን ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋን የሚመለከት ነበር።

"ለ1ኛ ተከሳሽ በመከላከያ ምስክርነት የተጠቀሰው እስክንድር ነጋ በከባድ ወንጀል የተከሰሰና በሽብርተኝነት የተፈረደበት ሲሆን ከዚህም በተጨማሪ ታስሮ በሚገኝበት ቃሊቲ ታራሚዎችን ለብጥብጥና ለረብሻ እያነሳሳና እያደራጀ ይገኛል። ስለዚህ ወደፍርድ ቤት ይዘነው ብንመጣ ለጥበቃችን፣ ለደህንነታችንና ለፖሊስ እጀባ ሥራ በጣም አደጋን ይፈጥራል። በመሆኑም በእነዚህ ምክንያቶች እስክንድርን ፍርድ ቤት ማምጣት የተቸገርን መሆኑን በማክበር እንገልጻለን" የሚለው የደብዳቤው ይዘት ነው።
[ዳኛው ይህንን ደብዳቤ በቅድሚያ ሲይዩ በአግራሞት ፈገግ ሲሉ ተስተውለዋል]

አቃቤ ሕግ በበኩሉ በዝዋይ ማረሚያ ቤት በቀረበው ደብዳቤ ላይ ተቃውሞ እንደሌለው፣ ነገር ግን ቃሊቲ ማረሚያ ቤት እስክንድር ነጋ ላይ ላቀረበው ምክንያት ፍርድ ቤቱ የራሱን ውሳኔ ይስጥ ሲል ተናገረ።

ጠበቃ አምሃም በዝዋይ ማረሚያ ቤት ጉዳይ ላይ ከአቃቤ ሕግ  የተለየ ሀሳብ እንደሌላቸው ጠቅሰው "እስክንድርን ነጋን በተመለከተ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ያቀረበው ምክንያት ለእኛ አሳማኝ አይደለም። ፍርድ ቤቱም መረጃ አለው ብለን አንገምትም።" ብለዋል።

አያይዘውም "እስክንድር አደረገ የተባለው ነገር  በማስረጃ የተደገፈ አይደለም። እስክንደር ለ1ኛ ተከሳሽ የሙያ ምስክር ናቸው። ከዚህ ቀደምም ካሉበት ቃሊቲ የሙያ ምስክር ሆነው ማረሚያ ቤቱ ፍርድ ቤት አቅርቧቸው ነበር። ደንበኛዬም እስክንድር እንዲመሰክርላቸው ሕገ መንግስታዊ መብት አላቸው። በዚህ ሁሉ ምክንያቶች የማረሚያ ቤቱ ምላሽ አጥጋቢና አግባብ አይደለም። በቀጣይ ቀጠሮ ማረሚያ ቤቱ ተገቢውን እጀባ አድርጉ እስክንድር ነጋን እንዲያቀርብልን ይታዘዝልን" ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል - ጠብቃ አምሃ።

አቃቤ ሕግም 2ኛ ተከሳሽ (አምሳሉ ገ/ኪዳን) በችሎት ባለመገኝታቸው ምክንያት ለዋስትና ያስያዙትን (20,000.00 ብር) ለመንግስት ገቢ ሆኖ በፖሊስ ተይዘው እንዲቀርቡ ጠይቆ ነበር።

ጥበቃ አምሃም አምሳሉ ትንናትን ጨምር በስልክ እንደተነጋገሩ በመጥቀስ፣ ከህመሙ የተነሳ ባሉበት ቦታ መንቀስቀስ እንዳልቻሉና በቀጣይ ቀጠሮ የሃኪም ማስረጃ እንደሚያቀርብ በድጋሚ ለችሎቱ አስረድተዋል።

ፍርድ ቤቱም የግራ ቀኙን ክርክር ካደመጠ በኋላ የዝዋይ ማረሚያ ቤት በቀጣይ ቀጠሮ ተመስገን ደሳለኝንና ውብሸት ታዬን እንዲያቀርብ በድጋሚ እንዲታዘዝ፣ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት እስክንድር ነጋን አስመልክቶ ያቀረበው ምክንያት በቂና አሳማኝ ባለመሆኑ በቀጣይ ቀጠሮ በቂ የፖሊስ አጃቢ አቅርቦ እንዲያመጣቸውና 2ኛ ተከሳሽም ከቀጠሮ በፊት ማሰረጃቸውን እንዲያቀርቡ፣ ካላቀረቡ ግን በቀጠሮ 24 ሰዓታት በፊት በፖሊስ ተይዘው ከታሰሩ በኋላ በቀጠሮ ቀን እንዲቀርቡ ትእዛዝ ሰጥቷል።

በተጨማሪም በፍቃዱ ሃይሉ፣ ፍጹም ማሞ፣ ፍቃዱ ማህተመወርቅና በሪሁን አዳነ ተጨማሪ መጥሪያ ሳታስፈልጋቸው ከላይ በተጠቀሰው የቀጠሮ ቀን እንዲገኙ በማለት ዳኛው ተናግረዋል።

Source: https://m.facebook.com/eliasgebru.godana/posts/1126766120742743

No comments:

Post a Comment