Saturday, December 5, 2015

ማስተር ፕላኑና ተቃውሞው፡- የፖሊሲ ግድፈቶችና የመፍትሄ ሀሳብ!


.
የሰሞኑ ርህራሄ የጎደለው የመንግስት እርምጃን የሚያሳዩ ዜናዎችና ምስሎችን ማየት እጅጉን ያማል፡፡ ገዢዎቻችን የህዝብን ቅሬታ በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት የሚባል ነገር ከራቃቸው ሰነባብተዋል፡፡ በውይይት ከያዙት አቅዋም የተመለሱበት ጊዜያት ጥቂት ቢሆንም፣ ከህዝብ ተቃውሞ ሲነሳ ተወካዮችን በማስመደብ እና ሽምማግሌዎችን በመላክ ድርድሮችና ውይይቶች ይደረጉ የነበሩበት ጊዜ ሩቅ አይደለም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በመንግስትም ላይ ሆነ በስሩ በሚያስተዳድራቸው ተቋማት ላይ ለሚነሱ ማንኛውም አይነት ተቃውሞዎች ዘግናኝ እርምጃዎች መውሰድን እንደ ብቸኛ አማራጭ ተያይዞታል፡፡ ከሰሞኑም በአዲስ አበባው ማስተር ፕላን ዙሪያ ለተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ ከአንደኛ ደረጃ እስከ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ድረስ እየተወሰደ ያለው ዘግኛኝ እርምጃ የስርአቱን ማን አለብኝነትና የአመራሩን ጭካኔ በግልፅ የሚያሳይ ነው፡፡
.
የተቃውሞው መንስኤ የሆነው የአዲስ አበባ አዲስ ማስተር ፕላን ይህን ያህል ደም ማፍሰሱና ለብዙ አካልና ንብረት መጉደል ምክንያት መሆኑ ያሳዝናል፡፡ ይህንኑ ፕላን ከአመት በፊት የትግበራ እንቅስቃሴውን በመቃወም በተነሳው ተቃውሞ በመንግስት ፀጥታ ሃይሎች በተወሰደ እርምጃ የብዙ ንፁሃን ህይወት ተቀጥፏል፡፡ በማስተር ፕላኑ ስር የተካተተው የኦሮሚያ አጎራባች ከተሞችን በአዲስ አበባ ስር የማካተት እቅድና በቦታው ላይ ሰፍሮ የሚገኘው ህዝብ እጣ ፈንታ አጣብቂኝ ውስጥ ገብቷል፡፡ እንደዚህ አይነት እቅድ ህገ መንግስቱ ያፀደቀውን የፌደራሊዝምን መርህ ጥያቄ ውስጥ ከማስገባቱም በላይ ሀገሪቱ የምትከተለው የከተማ ልማት ፖሊሲ ግድፈቶች ማሳያም ጭምር ነው፡፡ በዚህ ፅሁፍ የፖሊሲ ግድፈቶቹንና የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በአጭሩ ለመቃኘት ተሞክሯል፡፡
.
ያልተመጣጠነ የከተማዎች እድገት
.
አዲስ አበባ የሃገሪቱ ዋና ከተማ እና የትላለቅ አለም አቀፍ ድርጅቶች መቀመጫ እንደመሆኗ ከሌሎች ከተሞች በኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴም ይሁን በአገልግሎት አቅርቦቷ የተሻለች እንደምትሆን ቢጠበቅም አሁን እንደሚስተዋለው ከሌሎች ከተሞች አንፃር የተጋነነ ልዩነት መኖሩ የሃገሪቱን የከተማ ልማት ፖሊሲ ጥያቄ ውስጥ ያስገባዋል፡፡ ኢትዮጵያ ማለት አዲስ አበባ ማለት እስኪመስል ድረስ (ምናልባትም ከተወሰኑ የቱሪስት ከተማዎች ውጪ) የመንግስትም የህዝብም ንብረት፣ እውቀትና ገንዘብ አዲስ አበባ ላይ እየፈሰሰ ይታያል፡፡ ከሌሎች ከተሞች ጋር ያላት ልዩነትም እያደር በተጋነነ መልኩ እየሰፋ ይገኛል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ አዲስ አበባ እጅግ የተጨናነቀች ከተማ ሆናለች፡፡ የከተማዋ ኢንፍራስትራክቸር መሸከም ከሚችለው በላይ ህዝብ እያስተናገደ እንደሆነ የትናስፖርት፣ የገበያ፣ የጤና ተቅዋማት በመሳሰሉ የህብረተሰብ አገልግሎቶች መስጫ ቦታዎች ላይ የሚስተዋለውን ከመጠን ያለፈ ትርምስ እንደምሳሌ መውሰድ ይቻላል፡፡ ይሁንና የተሻለ የስራ እድል፣ የተሻለ አገልግሎቶች እና የተሻለ ብሩህ ተስፋ ይኖራል ተብሎ እስከታሰበ ድረስ ወደ አዲስ አበባ የሚደረገው ስደትም፣ ትርምስና መጨናነቁም ይቀጥላል፡፡
.
አንድ ሀገር እድገትን ማስመዝገብ ሲጀምር ከተማዎች ላይ የሚኖረው የህዝብ ቁጥር እየጨመረ ይመጣል፡፡ ስለዚህም የከተማዎች ማደግና መስፋፋት የአንድ ህዝብና ሀገር ተፈጥሮአዊ ሂደት ይሆናሉ፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ግን ሚዛናዊ የሆነ የከተማ እድገት ፖሊሲ እስካልተከተልን ድረስ በተለይ እንደኛ ፌደራላዊ ስርአትን እከተላለው በምትል ሀገር ላይ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ችግሮችን መፍጠሩ አይቀሬ ነው፡፡ አሁን የተከሰተው ተቃውሞም የዚህ ማሳያ ነው፡፡ ሌሎች ተወዳዳሪና አማራጭ ከተሞች እንዲመሰረቱ እና እንዲያብቡ፣ ላሉትም በቂ ድጋፍና ማበረታቻዎችን በማድረግ ማሳደግ እስካልተቻለ ድረስ ያልተመጣጠነ የከተማዎች እድገት በተወሰኑት ላይ ጫና በመፍጠር የቀውስ መንስኤ ከመሆን አይወገድም፡፡ መሪዎቻችን የአዲስ አበባ መስፋት የእድገታችን ትሩፋት መሆኑን ሲነግሩን ያልተመጣጠነ የከተማዎች እድገት ያስከተለው ፖሊሲያቸው ደግሞ ሀገሪቱ በታቀደ እና በተጠና መንገድ እየሄደች እንዳልሆነ እንደሚያሳብቅባቸው ልንነግራቸው ይገባል፡፡
.
ህዝብን ያላማከለ ከተሜነት
.
አንድ ገጠራማ የሆነ አካባቢ ወደ ከተማነት ለመቀየር የቦታው ባለቤት የሆኑትን ገበሬዎችንና የመሬት ባለቤቶችን ማፈናቀሉ አይቀሬ ነው፡፡ አዲሱ ማስተር ፕላንም በአዲስ አበባ አካባቢ ያሉ የኦሮሚያ ክልሎችን በስሩ ለማካተት ሲያቅድ ተመሳሳይ ነገር እንዲተገብር ይገደዳል፡፡ ሀብት ንብረቱን የሚያጣው የአካባቢው ነዋሪ በቂ ካሳ ሳይከፈለው ሲቀር ከፍተኛ ችግር ውስጥ ይገባል፡፡ በግብርና ለብዙ ትውልድ ሲተዳደር ለነበረ የህብረተሰብ ክፍል የንብረቱን ተመጣጣኝ የገንዘብ ካሳ ቢሰጠውም እንኳን ህይወቱን ሊለውጥ ይቅርና ባለበት ለማስቀጠል የሚያስችል ከግብርና ውጪ የስራ ክህሎት ይኖረዋል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ይህም ከተሜነቱ ሀብት ንብረቱን በማሳጣት የኑሮ ደረጃውን ወደታች የማሽቆልቆሉ እድል ሰፊ ያደርገዋል፡፡ ስለዚህም አይደለም እንደኛ ሀገር በቂ የንብረት ካሳ በማይሰጥበት ሀገር ይቅርና በቂ ካሳ ቢሰጥም እንኳን የገበሬውን ህይወት በነበረበት ለማስቀጠል ተጨማሪ መንግስታዊ ድጋፎችን ይሻል፡፡
.
ለዚህ አዋጭ የሆነው አማራጭ ካሳን በአግባብ ከመክፈል ባለፈ ህብረተሰቡ ሊደረግ በሚታቀደው ልማት ቀጥተኛ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻል ነው፡፡ የለውጡ መሪም፣ ተግባሪም፣ ተጠቃሚም መንግስትና በአካባቢው ያሉ አጃቢዎቹ ሲሆኑ ህብረተሰቡ የሚሰራው ልማት ለእሱ ጥፋት እንደሆነ ቢሰማው ተወቃሽ አይሆንም፡፡ የከተማዎች ግንባታ እንደሚታየው በወረራና በጅምላ በማፈናቀል ሳይሆን ከካሳ ክፍያው በተጨማሪ ህብረተሰቡን ጊዜ ሰጥቶና እድሎችን አመቻችቶ የመታዳደሪያ ምንጩን ከግብርና ወደ ሌላ አማራጮች እንዲቀይር በትምህርት፣ በስልጠና እና በፖሊሲ በመደገፍም መሆን አለበት፡፡ እንዲህ ሲሆን የከተሜነቱን ሂደት ቀድሞ የነበረውን ነዋሪ ያካተተ በማድረግ ጤናማ የሆነን ኢኮኖሚና ማህበረሰብን ለመገንባት ያግዛል፡፡
.
ህገ-መንግስታዊ እክል
.
ሀገራችን በፌደራላዊ ስርአት በተግባርም ባይሆን መተዳደር ከጀመረች ሃያ አምስት አመት ሊሞላት ነው፡፡ ፌደራላዊ ስርአት ሲባል የተለያዩ ራስ ገዝ የሆኑ አስተዳደሮች/ክልሎች በበጎ ፈቃድ አንድ ላይ ብንሆን የተሻልን እንሆናለን ብለው በማመን በጋራ ስምምነት ላይ የተመሰረተ የራስ ገዝ ግዛቶች ስብስብ ነው፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ባለው ህገ መንግስት ደግሞ ከብዙ ሀገራት በተለየ መልኩ የመገንጠልን ነፃነት መጨመሩ ክልሎችን የራስ ገዝ ደረጃ ከፍ ያደርገዋል፡፡ በክልሎች መካከልም ያለው ወሰን በሀገራት መካከል እንዳለ ወሰን ጠንካራ ያደርገዋል፡፡ በዚህ አግባብ ውስጥ የአዲስ አበባ አስተዳደርን የኦሮሚያ አዋሳኝ ከተሞችን በስሩ ለማካተት ማሰቡ በመርህ ደረጃ የሌለ ሀገርን ግዛቶች ከመውረር ጋር ተመሳሳይ ያደርገዋል፡፡ ስለዚህ አይደለም ገበሬዎችን ከይዞታቸው ያፈናቅላል፣ ገንዘብ ንብረት አልባ አድርጎ ወደ ድህነት ይወረውራቸዋል፣ በቂ ካሳ አይሰጣቸውም የሚሉ ክርክሮች የፕላኑ አተገባበር ፍትሃዊ በማድረግ ሊቀረፉ ይችላሉ፡፡ ከላይ የተጠቀሰው ህገ-መንግስታዊ እክል ግን በመርህ ደረጃ አዲስ አበባ እንደዚህ አይነት እቅድም ማውጣት እንደማትችል ያሳየናል፡፡
.
የመፍትሄ አቅጣጫ
.
አዲስ አበባ ታቅዶም ይሆን ሳይታቀድ እያደገችና እየሰፋች ያለች ከተማ መሆኗ ግልፅ ነው፡፡ የከተማዋ አጎራባች ከተሞችም ከከተማዋ ተርፎ እየፈሰሰ ያለው ከተሜነት በከፍተኛ ፍጥነት እየወረራቸው ይገኛል፡፡ ይህንን መስፋፋት መስመር በያዘና በታቀደ መልኩ እንዲፈስ ማድረጉ አስፈላጊነቱ አያጠራጥርም፡፡ በዚህ ሂደት ላይ ግን ያለው የአገሪቱ ፌደራላዊ አወቃቀርና ከዚህ በፊት የነበሩ የተመሳሳይ እቅዶች አፈፃፀም የነበራቸው መጥፎ አሻራዎች ከፍተኛ እክል ሆኖበት ይገኛል፡፡ በሀገሪቱ ለሁለተኛ ጊዜ የተቀሰቀሰውም ተቃውሞ በትክክልም ህገ መንግሳታዊ እና ሞራላዊ መሰረት እንዳለው ከዚህ አንፃር በግልፅ ማየት ይቻላል፡፡ የእንደዚህ አይነት ሁለት ፌደራላዊ ግዛቶችን የሚያካትት እቅድ በሁለቱ ከተሞች ህዝቦችና አስተዳደሮቻቸው ስምምነት እና ትብብር መተግበራቸው የግድ ይላል፡፡
.
ሁለቱ ክልሎች ተባብረውና ተናበው እስከሰሩ ድረስ የአዲስ አበባ አጎራባች ከተሞች የግድ አዲስ አበባ ውስጥ መካተት አለባቸው ማለት ህገ መንግስታዊ ድንጋጌዎችን ከመናዱም በላይ አላስፈላጊ ግትርነት ነው፡፡ የአካባቢዎቹን ልማት በኦሮሚያ ውስጥ ማድረጉ የሀገሪቱን የከተማዎች ስብጥር የተሻለ እንዲሆን የሚያደርገው ሲሆን አተገባበርም ላይ ህገ መንግስታዊ ድንጋጌን እንዳይጥስ ያደርገዋል፡፡ ከተሜነቱን ተከትሎ የሚገኘውም ገቢ በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ በክልሉ ውስጥ ለሌላ ልማታዊ ስራዎች ጥሩ የገቢ ምንጭ ይሆናል፡፡ ከዚህ መሰረታዊ ለውጥ በተጨማሪ በከተማ መስፋፋቱ ለሚፈናቀሉ ገበሬዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች በቂ ጊዜ በመስጠት ህይወታቸው መስተጓገል ሳይደርስበት ወደ አዲሱ ህይወት እንዲሸጋገሩ ማገዙ ግድ ይላል፡፡ ልማት ህግን አክብሮ እና ህዝብን ተጠቃሚ አድርጎ ሲመሰረት ዘላቂነቱም ቅቡልነቱም ሰፊ ይሆናል፡፡

No comments:

Post a Comment