Tuesday, December 29, 2015

በመሬት አስተዳደር ዙሪያ የሚሰሩ ባለሙያዎች ለመሬት ዝርፊያ ከፍተኛ አመራሮችን ተጠያቂ አደረጉ


ታኀሳስ ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በአማራ ክልል የሚገኙት ከፍተኛ የመሬት አስተዳደር ባለሙያዎችና የስራ ሂደት መሪዎች ለኢሳት እንደተናገሩት ‹‹ በእኛ ዘመን መሬት በየትኛውም አቅጣጫ በሙሰኞች እጅ መውደቁ ቁጭት ፈጥሮብናል፡፡ ››ይላሉ ፡፡ ትልቁን ሚና የሚጫወቱት የስርአቱ አመራሮች ናቸው ሲሉ ይወቅሳሉ።
ከአደርባይነት የተላቀቀ አመራር ማግኘት ከፍተኛ የወቅቱ ችግር መሆኑን የሚናገሩት የስራ ሃላፊዎች በተለይ መሬት በከተሞች ላይ ትልቅና ፈታኝ በሆነ መንገድ በግለሰቦች እጅ እየተጠቃለለ መሆኑን ይገልጻሉ፡
‹‹በፈጻሚው አካልም መሬትን በተገቢ መንገድ ለማስተላለፍ የሚታዩ ውስንነቶች አሉ ›› የሚሉት የስራ ኃላፊ ባለሙያዎች ከባለሃብቱ ጋር በመደራደር ካለ አግባብ ለመጠቃቀምና የድሃውን ህብረተሰብ ንብረት ለመንጠቅ የሚሰራ ስራ እንዳለ ይናገራሉ፡፡ የፍትህ አካሉ ከደላሎችና ከሙሰኛ ባለስልጣናት ጋር በመመሳጠር በመንግስት ክርክሮች ላይ ሁልጊዜም መሸነፍ እንደሚታይ የሚገለጹት ኃላፊው ይህም የስርዓቱ መሰረታዊ ችግር እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡
በተመሳሳይ ዜና የባህርዳሩ ሆምላንድ ሆቴል በአካባቢው የነበሩትን 62 አባዎራዎች ከመኖሪያ አካባቢያቸው በማፈናቀል በከተማዋ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ የ20 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ከከተማ አስተዳደሩ መቀበሉ ነዋሪውን እያነጋገረ ነው፡፡
በሆቴል ንግድ በክልሉ ከሚንቀሳቀሱ ባለሃብቶች በተለየ ሁኔታ ያለ በቂ ምክንያት ሰፊ መሬት የተሰጣቸው የሆቴሉ ባለቤት ፣ ለገዢው መንግስት ካላቸው ቀረቤታ አንጻር ልዩ ልዩ ስብሰባዎችንና ግብዣዎችን ያለ ጨረታ እንዲሰጣቸው መደረጉ አግባብ እንዳልሆነ በዘርፉ ተወዳዳሪ የሆኑ ባለ ሆቴሎች ቅሬታቸውን ይገልጻሉ፡፡
በባህርዳር ከተማ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው ነዋሪ 150 ካሬ ሜትር ቦታ በማጣት የመኖሪያ ቤት ችግር ላይ ባለበት ሁኔታ በከተማዋ ማዕከላዊ ቦታና ወደ አየር መንገድ በሚወስደው ሰፊ አስፓልት ዳርቻ የሚገኘው ይህ ሆቴል ፣ በሆቴል ማስፋፊያ ስም ቢሰጠውም በቦታው ላይ የሚገነቡት የሆቴሉ ተጨማሪ ህንጻዎች ደረጃቸውን ያልጠበቁ ከሁለት ፎቅ ያልበለጡ ተራ ግንባታዎች መሆናቸውን ፕላኑን የተመለከቱ የክልሉ ከፍተኛ ባለሙያዎች ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡
ከባህርዳር ዜና ሳንወጣ በከተማው የሚገኘው አባይ ድልድይ በተወሰነ ደረጃ የመስመጥ አደጋ በማጋጠሙ መኪኖች እስከ ግማሽ ሰዓት ድረስ ተራ እየጠበቁ ለማለፍ ተገደዋል፡፡ የግድቡ መበላሸት ያሳሰባቸው ነዋሪዎች ከአምና ጀምሮ ተደጋጋሚ አቤቱታዎችን ለኢሳት ሲልኩ ቆይተዋል።

No comments:

Post a Comment