Friday, September 25, 2015

በኬንያና ማላዊ ብቻ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በእስር ላይ ናቸው Posted by


መስከረም ፲፬ (አስራ አራት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-በኬንያ ኢዞሎ ግዛት ውስጥ ድንበር አቋርጠው ለመሻገር ሲሞክሩ የተያዙት ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች በተጨናነቀ እስር ቤት ውስጥ በስቃይ ላይ እንደሚገኙ ኦል አፍሪካን ዘግቧል።
በኬንያ ኢዞሎ ጂኬ እስር ቤት ውስጥ ከሚገኙት 450 እስረኞች መካከል 300 ዎቹ ኢትዮጵያዊያን ናቸው። እስር ቤቱ ከ 150 የበለጡ እስረኞችን መያዝ እንደማይችል የኢዞሎ ግዛት ምክትል ኮሚሽነር ገልጸዋል።
በኬንያ ውስጥ የሚገኙ ሕገወጥ ስደተኛ አዘዋዋሪዎችን አድኖ ለመያዝ እየሰሩ መሆኑን የገለጹት ባለስልጣኑ፣ የእስር ጊዜያቸውን የጨረሱ ሰማንያ ኢትዮጵያዊ እስረኞች ባለፈው ወር ወደ አገራቸው መጠረዛቸውንና መቶ ሃያ ኢትዮጵያዊያን ደግሞ በሜሩ ግዛት ውስጥ ፍርድቤት መቅረባቸውን አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት በእስር ላይ የሚገኙት ዜጎቹን ለማስለቀቅም ሆነ ለመጎብኘት ምንም ዓይነት ጥረት እስካሁን ድረስ አላደረገም።
በማላዊ እስር ቤት ውስጥ ደግሞ 387 እስረኞች ሲኖሩ፣ ሰላሳ ስድስቱ ኢትዮጵያዊያን እስረኞች በዓለማቀፉ የስደተኞች ድርጅት አይ ኦ ኤም አማካኝነት ወደ ትውልድ አገራቸው እንዲመለሱ ተደርገዋል።
ከተመለሱት መካከል ሕፃናት እንደሚገኙበትና በሽዎች የሚቆጠሩ ኢትዩጵያዊያን ስደተኞች በማላዊ አድርገው ሞዛምቢክና ዛምቢያን አቆራርጠው ወደ ደቡብ አፍሪካ በሕገወጥ መንገድ ይገባሉ።
በተጨማሪም የግብፅን ድንበር ጥሰው የሲና ባሕረ ሰላጤ የዋሻ መሸጋገሪያን በመጠቀም ወደ እስራኤል ሊገቡ ሲሞክሩ የነበሩ 22 ኢትዮጵያዊያንን ተይዘዋል። ከተያዙት መካከል የኤርትራ፣የግብጽ፣የሱዳን፣የኮሞሮስና የሶማሊያ ዜጎች ይገኙበታል።
የአውሮፓ ህበረት ስለሚሰደዱ ኢትዮጵያውያን ሰሞኑን ከኢህአዴግ ባለስልጣናት ጋር እየመከረ ነው።

Source:: Ethsat

No comments:

Post a Comment