Sunday, August 16, 2015

ሐብታሟ ምድር … የርሃብ ችግር (ከተማ ዋቅጅራ)

የአለማችን ጠበብቶች የሰው መገኛ ኢትዮጵያ እንደሆነች ብዙ ብዙ ብለዋል። እየሄድኩበት ያለሁት እንደ ሳይንስ ገለጻ እንጂ እንደ መጽሐፍ ቅዱስ እንዳልሆነ ይረዱልኝ ። ሳይንስ የምድርን እድሜ በሚሊዮን ሲቆጥር መጽሐፍ ቅድስ ደግሞ መሺዎች ይቆጥራል። እናም ስለ ድንቅነሽ (ሉሲ)ሳይንሱን ተከትዬ መግለጼን ልብ ይበሉልኝ።

ድንቅነሽ (ሉሲ) በኢትዮጵያ መኖር ከጀመረች ከሶስት ሚሊዮን አመት በፊት እድሜ እንዳላት ተመራማሪዎች ነግረውናል። በዚህም የተነሳ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ አገር እንደሆነች እና የሰው ዘር ከኢትዮጵያ ተነስቶ ወደ ተለያዩ የአለማችን ክፍሎች በመሄድ አሁን ያለውን የሰው ዘር ስብጥር እንደተፈጠረ ተመራማሪዎቹ ማስነበብ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። ድንቅነሽ (ሉሲ) ከአዲስ አበባ ሙዚዬም ተነስታ ወደ አሜሪካ በመውሰድ ትላልቅ የአለማችን ሰዎች እንዳዩአት እና ሳይንስቶችም ከፍተኛ ጥናት እንዳደረጉበት ይታወቃል። ድንቅነሽ (ሉሲ) ለምን መሄድ አስፈለጋት? ያስገኘችውስ ፖለቲካዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳስ ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ የኢትዮጵያ ህዝብ ሲገለጽልን ሰምተን አናውቅም። የሆነው ሆኖ በጉብኝቷ ወቅት ያስገኘችው ገቢ ቀላል የሚባል እንዳይደለ ይታወቃል። በትንሹ ለክልሉ ተወላጆች ሃምሳ የውሃ ጉድጓድ በስሟ አስቆፈረው ህብረተሰቡ እንዲጠቀም ቢደረግ በተወሰነ መልኩ የሚታየውን የውሃ እጥረት መቅረፍ በቻለ ነበረ።

ኖርዌይ ያራ የሚባለው ካንፓኒ ከአፋር ምድር ፖታሽ (potash) ለማውጣት ከገዚው ፓርቲ ተፈራርመዋል። የማጓጓዛዋ አገር በጅቡቲ ወደብ እንደሆነ ታውቋል። ከፖታሹ ብዛት የተነሳ የኖርዌይ የማዕድን አውጪ ካንፓኒ አጋር አገር እያፈላለገ እንደሆነ ተዘግቧል። ስራውን ሲጀምር በየአመቱ ከፍተኛ ፖታሽ (potash) እንደሚያወጣ አሳውቆናል። ለአገር ገቢ ከፍተኛ አስተዋጾ ያደረገች አፋር ከሚገኘው ገቢ መትንሹ መቶ የውሃ ጉድጓድ ተቆፍሮ ለህብረተሰቡ ቢሰጣቸው ኖሮ እንስሳታቸውም አይሞቱም አገሪቷም በድርቅ ምክንያት ከሚመጣው ችግር ባልተጋለጠች ነበረ። በሚገኘው ገቢ የግለሰብ ኪስ ሲሞላ እንጂ የህብረተሰቡ ኑሮ ሲሞላ አላየንም። የግለሰቦች ሃብት ሲጨምር እንጂ የአገር ሃብት ሲጨምር አላየንም። አፋር ላይ ያየነውም የዚህ ነጸብራቅ ነው።

በድስ ውስት ሆና እንደምትተንተከተክ ሽሮ በኤርታሌ የሚታየው የሳተ ጎሞራ ሁኔታ የሚያሳየን ይሄንኑ ነው። ተመራማሪዎችን ትኩረት የሳበ ስለ እሳተ ጎሞራ ባህሪ ለማጥና ከአለማት የሚመጡባት አገር ናት። ቱሪዝምን በመሳብ በድንቅ ተፈጥሮዋ በብዙ ጎብኚዎች የምትጎበኘው ምድር ከቱሪዝም ከሚገኘው ፍሰት ለአካባቢው ነዋሪዎች የሚያስፈልጋቸው ቀዳሚ ነገር የውሃ ፍላጎታቸው ተሟልቶ ቢሆን ኖሮ ዛሬ የተከሰተው ድርቅን ባላየን ነበረ።

የአሞሌ ጨው ክምር ሜሬት ላይ ተነጥፎ በቀላሉ ተቆፍሮ የሚወጣባት አገር ሁሉ ነገር ኖሯት ሃብታም ሆና ሳለ ምንም እንደሌላት በውሃ እጦት እንሰሳዎቿ በውሃ እጦት ሲረግፉባት ማየት ለኢትዮጵያን ሞት ነው።

ጅቡቲን ውሃ ለማጠጣት የውሃ ጉድጓድ በመቆፈር ያውም በነጻ ሲለግስ የሱማሌ ክልል ምድሪቷ ሃብት ኖሯት ውሃ ተጠማን እያሉ መስማት ለኢትዮጵያን የሚያም ጉዳይ ነው። የአልሙኒዬም መአድን እንዲሁም የጋዝ ክምችት ያላት አገር ለወገን አሳቢ መንግስት ስሌለ ብቻ የኢትዮጵያ ልጆች ማደግ ስንችል መበልጸግ ሲኖርብን ከራሳችን አልፈን ሌሌላው የሚተርፍ ስራ መስራት እየቻልን የአገሩን ዜጋ ሳያጠጣ ለጎረቤት አገር በነጻ የሚሰጥ መንግስት በመኖሩ …በውሃ እጦት እንስሳታቸው እየሞቱባቸው ነው? ዜጎች ከፍተኛ አደጋ ላይ ናቸው? የሚለው ጥያቄ ህዝብን እንጂ መንግስትን የሚያሳስበው ጉዳይ እንዳልሆነ ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነው።

የወያኔ መንግስት ስለ ኢትዮጵያ ህዝብ ህይወት የሚጨነቅ ወይም የሚያስብ ሳይሆን ከውጪ መንግስታት ስለሚያገኘው ጥቅማ ጥቅም ወደ ግል ካዝናቸው የሚገባበትን ጉዳይ አብዝተው የሚጨነቅ ስለሆኑ ስለ ኢትዮጵያ ህዝብ ምንም ሃላፊነት የሚሰማው ስላልሆኑ ህዝባችን በተለያየ አካባቢ ከፍተኛ ችግር እየተጋለጠ ይገኛል። አንድ ቢሊዮን ዶላር በማውጣት የነጻ ሚድያዎችን እና ዌብ ሳይቶችን ለማፈን ወጪ ከምታደርጉ ይልቅ በዚህ ብር የዝናብ እጥረት የሚታዩበትን የኢትዮጵያ አካባቢዎች የውሃ ጉድጓድ ለህዝቡ ቢዳረስ ኖሮ ከእንደዚህ አስከፊ የድርቅ ችግር ሆነ የእንስሳት እልቂት ባልተከሰተ ቀድሞ መቆጣጠር በተቻለም ነበረ። ከሁሉ በፊት ስለ ህዝብ አስቡ! ከሁሉ በፊት ስለ ሰው ክብር እወቁ! ከሁሉ በፊት ስለ ግለሰብ መብት እንዲከበር ስሩ! ከሁሉ በፊት ስለ አገር ክብር ስለ ህዝብ ችግር ቀደሞ ለመገኘት ጣሩ እላለው። ለነገሩ ህዝብና መንግስት በሃሳብም ሆነ በማንኛውም ነገር አልተገናኝቶም።

ከተማ ዋቅጅራ

16.08.2015

Email- waqjirak@yahoo.com

Source : Zehabesha

No comments:

Post a Comment