Friday, June 19, 2015

ምርጫውን ተከትሎ በኦሮምያ ብቻ ከ600 በላይ የመድረክ አባላት ታስረዋል


ሰኔ ፲፪ (አስራ ሁለት) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- በብዙዎች ዘንድ አስቂኝ ተብሎ የተተቸውን የ2007 ዓም ምርጫ ተከትሎ በኦሮምያ ብቻ ከ640 በላይ የመድረክ ደጋፊዎች ሲታሰሩ፣ 66 በድብደባ ጉዳት ደርሶባቸዋል፣7 አባለት በጥይት ቆሰልዋል፣ 2 አባላት ደግሞ መገደላቸውን መድረክ አስታውቋል። ከምርጫው ጋር በተያያዘ የሚታሰሩ ሰዎች ቁጥር በሺዎች እንደሚቆጠር መረጃዎች ያመለክታሉ።
መድረክ እንዳለው በምርጫ 2007 ማግሥት በመድረክ አባላት ላይ የሚፈጸሙት የማዋከብና የማሰቃየት ተግባራትም እየተባባሱ ነው።
በምዕራብ ትግራይ ዞን የአረና/መድረክ የድርጅት ጉዳይ ኃላፊ ሆነው በ2007 ምርጫ ወቅት በዞኑ የምርጫውን ሥራ በማደራጀትና በመቀስቀስ እንደዚሁም ታዛቢዎችን በመመደብ ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ የቆዩት አቶ ታደሰ አብርሃ አርአያ በመኖሪያ
ቤታቸው ተደብድበው መገደላቸውን መድረክ ጠቅሷል። አቶ ታደሰ ሰኔ 9 ቀን ከምሽቱ 3፡00 ሰዓት ላይ ለጊዜው ማንነታቸው በግልጽ ተለይቶ ባልታወቁና ወደ ቤታቸው በመጡ 3 ሰዎች በተፈጸመባቸው አሰቃቂ ድብደባ ሕይወታቸውን ያጡ ሲሆን፣ በምርጫው ቅስቀሳ ወቅት በኢህአዴግ ካድሬዎችና ታጣቂዎች ድብደባ የተፈጸመባቸው ከመሆኑም በላይ ምርጫው ሲያልፍ አንድ በአንድ እንለቅማችኋለን፣ የትም አታመልጡንም የሚል ዛቻና ማስፈራሪያ ደርሶባቸው እንደነበረም ገልጿል።
በትግራይ ከምርጫው ጋር በተያያዘ በመቀሌ ወይኒ ቤት የታሰሩ 17 አረና መድረክ አባላት መኖራቸውንም ገልጿል።
በደቡብ ክልል በጋሞጎፋ ዞን በአርባ ምንጭ የምርጫ ክልል የላካ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑትና የመድረክ ወኪል/ታዛቢ የነበሩት የአቶ ዳንኤል ጉዴ ቤት ሰኔ 8፣ 2007 ዓም ከሌሊቱ 8፡00 ሰዓት ላይ ቤተሰባቸው በውስጥ እያለ ከውጭ በኩል ተዘግቶ እንዲቃጠል ተደረጎ በህዝቡ እርዳታ የቤተሰቡ ሕይወት ሲተርፍ ቤቱና በቤቱ ውስጥ የነበረው ንብረት መውደሙንም ፓርቲው አስታውቋል።
ቃጠሎው ከመፈጸሙ በፊት ከቀኑ በ9፡00 ሰዓት ላይ አቶ ዋቻ ዋዛ የተባሉ የቀበሌው የፍትሕና ጸጥታ ኃላፊ፣ አቶ ደበበ ዴሶ የኢህአዴግ የመሠረታዊ ድርጅት አመራር አባል፣ አቶ ካፍቴ ካልሌ የቀበሌው አስተዳዳሪ፣ አቶ ኦቾ አሮቤ የቀበሌው ሥራ እስኪያጅ፣አቶ ማስታ ጉሜ የቀበሌው ንዑስ ቡድን መሪ ከወረዳው ከመጣው ዛጋ ዘለሎ ከሚባሉ የፖሊስ ባልደረባ ጋር ሆነው የአቶ ዳንኤልን ቤት እንደሚያቃጥሉ የዛቱ ሲሆን በወላጅ እናታቸው በወይዘሮ ሐማሜ ሔጃ ላይም አቶ ማስታ ጉሜ በሚባሉ የቀበሌው ንዑስ ቡድን መሪ እና በልጃቸው በአቶ መላኩ ማስታ አማካይነት በዚሁ ዕለት ድብደባ እንደተፈጸመባቸውና ከፍተኛ ጉዳት እንዳደረሱባቸው መድረክ ገልጿል።
የአከባቢው ሕዝብ ድብደባ የደረሰባቸውን እናት ወደ ሐኪም ቤት ተሸክመው ለማድረስ ሲሞክሩም፣ ዛጋ ዘለሎ የተባሉት ፖሊስ እንደከለከሉ የገለጸው ፓርቲው፣ በአሁኑ ወቅትም የአቶ ዳንኤል ቤተሰብ አባላት ያለአንዳች ንብረትና መጠለያ ሜዳ ላይ ቀርተዋል ብሎአል።
በዚሁ ዞን በደራማሎ ወረዳ ምርጫ ክልል 22 የመድረክ አባላትና ደጋፊዎች ሕዝብን በመንግሥት ላይ አነሳስታችኋል በሚል ክስ የአራት ወራት እስራት የተፈረደባቸው ሲሆን ፣ ሌሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ላይ ደግሞ ተመሳሳይ ክስ ተመሥርቶባቸው ጉዳዩ በሂደት ላይ ነው። እስራቱ ከተፈረደባቸው ሰዎች 18ቱ ለእስረኞች የሚሰጥ ምንም ምግብ በሌለበት በወረዳው ፖሊስ ጣቢያ ታስረው በረሀብ እየተጎዱ መሆኑንም መድረክ ገልጿል።
በአርባ ምንጭ ምርጫ ክልል በላካ ምርጫ ጣቢያ ደግሞ የቀበሌው አመራር አባለትና ታጣቂዎች ከወረዳው ከተመደቡ ሀብታሙ በቀለ እና ዘጋ ዘለሎ ከሚባሉ ሁለት ፖሊሶች ጋር ሆነው ኢህአዴግን ተቃውማችሁ መድረክን መርጣችኋል ያሉዋቸውን ስድስት የቀበሌው ነዋሪዎችን ማለትም አቶ ገርማ ጋርሶ፣ አቶ ቦርካ ይሎ፣ አቶ ቤልጅግ ሣሮ፣ አቶ አንብርጎ አብፅ፣ አቶ ዳማ ዳላላ እና አቶ ሣንሴ ሣጋሌ የተባሉትን ሌሊት ወደ ቀበሌ ጽ/ቤት ወስደው ክፉኛ በመደብደብ አሰቃይተው መድረክን መደገፋቸውን ካላቆሙ እንደሚገድሉዋቸው በመዛት መልቀቃቸውን መድረክ ገልጿል።
በዛይላ ወረዳ ምርጫ ክልል ደግሞ አቶ ደሳለኝ ደቡሎ ከቦላ ቀበሌ፣አቶ አይነቴ አዛዜ ከዛይላንዴ ቀበሌ የአራት ወራት እስራትና የ200 ብር ቅጣት የተወሰነባቸው ሲሆን፣ ሌሎች ከ30 በላይ አባላት ደግሞ ከምርጫው ዕለት በፊት ከተለያዩ
ቀበሌዎች ተይዘው በወረዳው ፖሊስ ጣቢያ እንዲታሰሩ ከተደረጉ በኋላ ምርጫው ሲጠናቀቅ በ18/09/2007 ተለቅቀዋል፡፡
በኦሮምያ ቀበሌዎች የመድረክ አባላትና ደጋፊዎች ሆነው በምርጫው የተንቀሳቀሱ ዜጎችን ለመበቀልና ለወደፊቱ ከእንቅስቃሴያቸው እንዲገቱ ለማድረግ በቀበሌ ሊቃነመናብርት የሚመራና የቀበሌ ካቢኔ አባላት የሚገኙበት የሰላም ቦርድ የሚባል አካል ተቋቁሞ በመድረክ አባላትና ደጋፊዎች ላይ ከፍተኛ የገንዘብ ቅጣት በመጣልና በማስከፈል ላይ እንደሚገኝ የገለጸው መድረክ፣ ይህንን ህገ-ወጥ ቅጣት በመቃወም ዜጎቹ ለየአከባቢያቸው ፖሊስ ጣቢያዎች ለሚያቀርቧቸው አቤቱታዎችም ከቀበሌ የሰላም ቦርድ የድጋፍ ደብዳቤ ካላመጣችሁ አቤቱታችሁን አንቀበልም እየተባሉ እንደሚባረሩ ፓርቲው አስታውቋል።
በኦሮምያ፣ በደቡብ፣ በአማራ፣ በትግራይና በአዲስ አበባ ከምርጫው ጋር በተያያዘ የታሰሩት ሰዎች ቁጥር በሺ እንደሚቆጠር መረጃዎች አመልክተዋል። ገዢው ፓርቲ ምርጫውን መቶ በመቶ አሸንፌአለሁ ቢልም አብዛኛው ህዝብ አልተቀበለውም። የገዢው ፓርቲ የበቀል ጅራፍ አስመርሯቸው አገራቸውን ጥለው እየተሰደዱ፣ በትጥቅ ትግል የሚታገሉ ድርጅቶችን የሚቀላቀሉ ወጣቶች ቁጥር ከእለት እለት እየጨመረ ነው።

1 comment: