Monday, March 30, 2015

በጋምቤላ ሌላ ዙር የጎሳ ግጭት አንዣቧል ሲሉ የጋምቤላ ኒሎትስ አንድነት ንቅናቄ አደራጅ ተናገሩ

መጋቢት ፳፩(ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፯ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-የንቅናቄው መስራችና አደራጅ ከኢሳት ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደገለጹት የህዝባዊ ወያን ሃርነት ትግራይ መንግስት በአካባቢው ያለውን መሬት ሙሉ በሙሉ ጠቅልሎ ለመውሰድ ባለው ፍላጎት
በአኝዋኮችና በኑወር ብሄረሰቦች መካከል ግጭት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ ነው። ኑወሮችን በጦር መሳሪያ ከማስታጠቅ ጀምሮ ከደቡብ ሱዳን የሚፈናቀሉ ኑዌሮች በአኝዋኮች፣ መዠንገሮችና ሌሎች ብሄረሰቦች መካከል እንዲሰፍሩ በማድረግ እስከዛሬ የነበረውን
የህዝብ አሰፋፈር በመቀየር አዲስ ግጭት ለምፍጠር ይቀሳቀል በማለት አቶ ኦኮክ ክስ አቅርበዋል።
በመጋቢት ወር 2 አኝዋኮች መገደላቸውንና 3 ደግሞ መቁሰላቸውን እንዲሁም በርካታ ሴቶች እና ህጻናት ከ ፒንዩዶ የስደቶች ካምፕ ታፍነው መወሰዳቸውን ፣ በየካቲት ወር ደግሞ 2 ህጻናት ታፍነው ሲወሰዱ፣ አንድ የአኝዋክ አርሶ አደር ደግሞ ተገድሏል። በኩትቡዲ
ፒንዩዶም እንዲሁ 4 አኝዋክ ህጻናት ታፍነው ሲወሰዱ፣ የኒዩም መንደር አዣዥ ኦጉልም እንዲሁ ተገድለዋል።
ከአሁን በፊት በተቋቋሙት ቦንጋ፣ ዲማ፣ ፒኑዩዶ እና አኩላ ወይም ኢታንግ የሰፈራ ጣቢያዎች የገቡት የደቡብ ሱዳን ስደተኞች አልበቃ ብሎ በአኝዋክ፣ መዠንገር፣ ኦፖ እና ኮሞ ጎሳዎች መሬቶች ላይ ቾላን፣ ፖኮንግ፣ ጃዊ፣ ኦቾም፣ ኮቦን፣ ካራሚ የተባሉ አዳዲስ የሰፈራ
ጣቢያዎች መቋቋማቸው ሆን ተብሎ ግጭት ለመፍጠር መሆኑንና ምልክቶችም በመታየት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
ዋናው አላማው በክልሉ የሚታየውን መሬት ለመቀራመት መሆኑን የሚገልጹት አቶ አኮክ ፣ ሁለቱ ብሄረሰቦች በሚጋጩበት ጊዜ ተጠቃሚዎቹ መሬቱን የሚዘርፉት የህወሃት ሰዎች ናቸው ብለዋል።
በቅርቡ ከ80 በላይ አኝዋኮችና 45 መዠንገሮች በማእከላዊ እስር ቤት ታስረው እንደሚገኙ፣ የቀድሞውን የክልሉን መሪ አቶ ኦኬሎ አኳይን ጨምሮ ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ በርካታ አኝዋኮች ከደቡብ ሱዳን ጁባ ወደ ኢትዮጵያ ተላልፈው መሰጠታቸውን
ገልጸዋል። በክልሉ እየደረሰ ያለው ጭፍጨፋ በአጼ ሃይለስላሴ እና ደርግ ከነበረው ጋር ሲተያይ አስከፊ መሆኑን የገለጹት ሃላፊው፣ በዚህ ቀጠለ ለዘመናት መስዋትነት የከፈልንላትን አገራችንን እንዳናጣት ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
የሼክ አላሙዲን ሳውዲ ስታር ሳይቀር የመከላከያ ካምፕ መሆኑም አቶ ኦኮክ ገልጸዋል። ከአቶ አኮክ ጋር የተደረገው ቃልምልልስ ሰሞኑን ይቀርባል።

No comments:

Post a Comment